የአሜሪካው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ የአገራቸው ጦር የኢራን ዋነኛ የነዳጅ ዘይት መናኸሪያ የሆነውን የካርግ ደሴት ሊይዝ እንደሚችል ፍንጭ ሰጡ፡፡
- 2 days ago
- 2 min read
መጋቢት 21/2018 - የውጪ ሀገራት ወሬዎች
የአሜሪካው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ የአገራቸው ጦር የኢራን ዋነኛ የነዳጅ ዘይት መናኸሪያ የሆነውን የካርግ ደሴት ሊይዝ እንደሚችል ፍንጭ ሰጡ፡፡
የካርግ ደሴት የኢራን ዋነኛ የነዳጅ ዘይት ማምረቻ እና ለውጭ ገበያ ከታለመው ነዳጅ 90 በመቶው የሚላከው ከዚሁ ደሴት እንደሆነ ቢቢሲ ፅፏል፡፡
ከወር በላይ ባስቆጠረው የኢራን ጦርነት ምክንያት በአለም ዙሪያ የነዳጅ ዘይት ዋጋ በጣሙን እያሻቀበ ነው ተብሏል፡፡

ኢራን በኢስፍሐን ዩኒቨርስቲ ላይ ለተፈፀመባት ጥቃት በእስራኤል እና በባሕረ ሰላጤው አገሮች በሚገኙ የአሜሪካ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ላይ የአፀፋ ጥቃት እንደምታደርስ ዝታለች፡፡
ኢራን በእስራኤል ደቡባዊ ክፍል የኢንዱስትሪዎች መገኛ ላይ በፈፀመችው የሚሳየል ድብደባ ከባድ ቃጠሎ መድረሱ ታውቋል፡፡
ሰዎች ለመርዛማ ጢስ እንዳይጋለጡ ምክር እና ማስጠንቀቂያ እንደተሰጣቸው ተሰምቷል፡፡
ኢራን በቀጠናው እንደ ኩዌት ፣ ሳውዲ አረቢያ እና ባሕሬን ባሉ አገሮች ላይ የሚሳየል እና የድሮን ጥቃት መፈፀሟ ተጠቅሷል፡፡
ጦርነቱ በተፋፋመበት አጋጣሚ የፓኪስታን ሹሞች ኢራን እና አሜሪካን ስለ ሰላም ለማደራደር ተዘጋጅተናል ፤ እሺታቸውንም አግኝተናል ማለታቸውን መረጃው አስታውሷል፡፡
የኢራን ፓርላማ አፈ ጉባኤ ባጌር ጋሊባፍ የአሜሪካ ወታደሮች በእግረኛ ከመጡብኝ አናስተርፋቸውም አሉ፡፡
አፈ ጉባኤው የአሜሪካ ወታደሮች በምድር ወደ ግዛታችን ከዘለቁ ተዋጊዎቻችን እንደ አመጣጣቸው ይቀበሏቸዋል ማለታቸውን ቢቢሲ ፅፏል፡፡
የኢራኑ አፈ ጉባኤ አስተያየት የተሰማው አሜሪካ የላከቻቸው 3500 የልዩ ተልእኮ ወታደሮች በጦር መርከብ ተጓጉዘው በቀጠናው ደርሰዋል መባሉን ተከትሎ ነው፡፡
በቅርቡ የአሜሪካው የጦር ሚኒስትር ለኢራኑ ጦርነት ያስቀመጥነውን ግብ ያለ አንዳች የምድር ጦርነት እናሳካለን ብለው ነበር፡፡
ያም ሆኖ አሜሪካ በኢራን የምድር ጥቃት መክፈቷ አይቀርም የሚለው ወሬ በሰፊው እየተናፈሰ ነው፡፡
እስራኤል እና አሜሪካ በኢራን ላይ ጣምራ የጦር ድብደባ ከጀመሩ ከወር በላይ ሆኗቸዋል፡፡
ኢራንም በእስራኤል እና በቀጠናው አገሮች የአሜሪካውያን መገናኛዎች ናቸው ያለቻቸውን ሁሉ በአፀፋ ጥቃቷ እየመታች መሆኑን መረጃው አስታውሷል፡፡
በአፍጋኒስታን ያጋጠመ ከባድ ጎርፍ እና የመሬት መንሸራተት አደጋ 17 ሰዎችን ገደለ ተባለ፡፡
በአደጋው ሕይወታቸው ማለፉ ከተረጋገጠው በተጨማሪ ሌሎች 26 ሰዎች ደግሞ የተለያየ ደረጃ አካላዊ ጉዳት እንደገጠማቸው አሶሼትድ ፕሬስ ፅፏል፡፡
ጎርፉ እና የመሬት መንሸራተቱ በአገሪቱ ማዕከላዊ ፣ ምዕራባዊ እና ሰሜናዊ ምዕራብ ክፍሎች ማየሉ ታውቋል፡፡
አደጋው 150 ያህል ቤቶችን ሙሉ በሙሉ እና በከፊል ማውደሙ ተጠቅሷል፡፡
ከጥቂቱ ወራት በፊትም በአገሪቱ የደረሰ መሰል አደጋ በአስራዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን እንደገደለ መረጃው አስታውሷል፡፡
የየመን ሁቲዎች የቀይ ባህሩን የባብኤል መንደብ የባህር መተላለፊያ ሰርጥን ሊዘጉት ይችላሉ ተባለ፡፡
ባብኤል መንደብ የኤደን ባህረ ሰላጤ እና የቀይ ባህር መገናኛ ጠባብ የባህር መተላለፊያ ነው፡፡
ሁቲዎቹ ባብኤል መንደብን ሊዘጉት እንደሚችሉ አንድ ከፍተኛ ሹማቸው እንደተናገሩ ሚድል ኢስት ሞኒተር ፅፏል፡፡
ከትናንት በስቲያ እና ትናንት ሁቲዎቹ በእስራኤል ላይ የሚየል ጥቃት መሰንዘራቸውን መረጃው አስታውሷል፡፡
የሁቲዎቹ መሪ አብዱል መሊክ አል ሁቲ ኢራን በአሜሪካ እና በእሰራኤል ጣምራ ድብደባ እየተመታች እኛ እጃችን አጣጥፈን አናይም ያሉት ሰሞኑን ነው፡፡
በእስራኤል ላይ የሚሳየል ጥቃት መሰንዘራቸው የግጭቱ አካላት ስለመሆናቸው ፍንጭ ሰጭ ሆኗል፡፡
የኔነህ ከበደ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
X :- https://x.com/shegerfm?s=2
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7




Comments