የንግድ ህጉን ተላልፈው ተገኝተዋል ያላቸውን ከ24 ሺህ 500 በላይ ነጋዴዎች መቅጣቱን የንግድ ቢሮ ተናገረ።
- 1 hour ago
- 1 min read
ሐምሌ 21 2018
የንግድ ህጉን ተላልፈው ተገኝተዋል ያላቸውን ከ24 ሺህ 500 በላይ ነጋዴዎች መቅጣቱን የንግድ ቢሮ ተናገረ።
ቢሮው የ2018 ዓ.ም የእቅድ አፈፃፀሙን በገመገመበት ወቅት የቢሮ ሃላፊዋ ወ/ሮ ሃቢባ ሲራጅ ነጋዴዎቹን ለቅጣት ያበቃቸው ያለ ንግድ ፈቃድ መነገድ፣ ባልታደሰና በተሰረዘ ንግድ ፈቃድ መነገድ ጭምር መሆኑን ተናግረዋል።

የንግድ ህጉን አክብሮ ያለመስራት በዚህ ዓመትም ችግር ሆኖ ቀጥሏል የሚሉት ሃላፊዋ ከተቀጡት ነጋዴዎች አብዛኞቹ የፈጠሩትን ችግር እስከሚያስተካክሉ ድረስ የማሸግና ማስጠንቀቂያ የመስጠት ነው፤ በዚህም ከ24 ሺህ 500 በላዩ 90 በመቶዎቹ አስተካክለው ወደ ስራቸው ተመልሰዋል ብለዋል።
ይሁንንና አሁንም ያለ ንግድ ፈቃድ መነገድ፣ ኪሎ ቀንሶ መሸጥ፣ ባዕድ ነገሮችን መቀላቀልና ሌልውም ችግር ሆኖ መቀጠሉንና በመጪው ዓመት ለውጥ ለማምጣት እንደሚሰራበት ወ/ሮ ሃቢባ አንስተዋል።
በተጨማሪም በአዲስ አበባ የነዳጅ ማደያዎች በሚሸጡት ነዳጅ ላይ በሊትር ቅሸባ በማድረግ በነዳጅ ላይ ሊትር ቀንሰው የሚሸጡ ማደያዎች ተበራክተዋል፤በተደረገው የቁጥጥር ስራ 93 ማደያዎች ማስጠንቀቂያ ሲሰጣቸው 3 ማደያዎች ቅሸባን ሲፈፅሙ እጅ ከፍንጅ ተገኝተው ክስ ተመስርቶባቸዋል ፤ሌሎች 3 ማደያዎች ደግሞ ለ3 ወር ነዳጅ እንዳያገኙ ታግደዋል መባሉን ሰምተናል፡፡
በአዲስ አበባ በቢሮው ተመዝግበውና ፈቃድ ወስደው እየሰሩ ያሉ ነጋዴዎች ቁጥር 470 ሺህ ደርሷል፡፡
በዓመቱ ንግድ ፈቃዳቸውን የመለሱ ነጋዴዎች 10 ሺህ የሚጠጉ መሆናቸውን የጠቆሙት የቢሮ ሃላፊዋ አብዛኞቹ ዘርፍ የቀየሩ መሆናቸውንና ካለው የነጋዴ ቁጥር አንጻር ከንግድ ሥርዓቱ የመጣው 10 በመቶ የማይሞላ በመሆኑ ጥቂት የሚባል ስለመሆኑም አስረድተዋል፡፡
እንደ አጠቃላይ የምርት አቅርቦት ላይ በጣም የተሻሻሉ ነገሮች አሉ የሚሉት የንግድ ቢሮ ሃላፊ ሃቢባ ሲራጅ በከተማዋ በቢሮው በኩል በተቋቋሙ 7 የገበያ ማዕከላት እንዲሁም 264 በደረሱት የቅዳሜና እሁድ ገበያዎች በተለይ የግብርና ምርቶች እንደልብ እየቀረበ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ይሁንና በዓመቱ ከውጭ የሚገቡ የኢንዱስትሪ ምርቶች እጥረት ነበር በተለይ በምግብ ዘይት ምርት ላይ እጥረት በመኖሩ የዋጋ ንረት አሁንም አለ፤ እንደ ሽንኩርት ዓይነት ምርቶች እጥረት በመኖሩ ዋጋቸው መውጣትና መውረድ አለ፤ የኢንዱስትሪ ምርቶችን እጥረትን ለማቅለል እንሰራለንም ብለዋል፡፡
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ...
ምንታምር ጸጋው
_edited.jpg)



Comments