ዓለም እንድትቀጥል አንዲት ሴት በሕይወት ዘመኗ 2.1 ልጅ እንድትወልድ ቢያስፈልግም፣ አሁን ያለው ግን 1.1 መሆኑን ጥናት አሳየ።
- 2 hours ago
- 2 min read
ሐምሌ 21 2018
ዓለም እንድትቀጥል አንዲት ሴት በሕይወት ዘመኗ 2.1 ልጅ እንድትወልድ ቢያስፈልግም፣ አሁን ያለው ግን 1.1 መሆኑን ጥናት አሳየ።
የዓለም የሕዝብ ዕድገት ምጣኔ እያሽቆለቆለ መምጣቱን ያሳየውን ጥናት ያጠናው የተባበሩት መንግሥታት የሥነ ሕዝብ ተቋም ወይም UNFPA ነው።
UNFPA የዓለም የሥነ ሕዝብ ቀንን በማስመልከት፣ ትዳር የመመሥረት፣ ልጅ የመውለድ የመሳሰሉ የወጣቶች ፍላጎቶችን በተመለከተ ያጠናውን ጥናት አዲስ አበባ ላይ ይፋ አድርጓል።
ጥናቱ 73 አገሮችን እና ዕድሜያቸው ከ18 እስከ 39 ዓመት የሆኑ 108 ሺህ ወጣቶችን በመጠየቅ እንደ ተጠናቀቀም ተነግሯል።
የጥናቱ ውጤትም ዓለም እንድትቀጥል አንዲት ሴት በሕይወት ዘመኗ መውለድ ከሚጠበቅባት በግማሽ ያነሰ እየወለደች መሆኑን ማሳየቱን፣ በUNFPA የወጣቶች ተሟጋች ቤዛዊት እድሉ ነግራናለች።
የወሊድ ምጣኔ እየቀነሰ መሆኑን ጥናቱ አሳይቷል፤ 2.1 ነው ዓለም እንዲቀጥል የውልደት ምጣኔ የሚያስፈልገው።

አንዲት ሴት ልጅ 2.1 በስታቲስቲክስ መሠረት መውለድ አለባት ተብሎ ነው የሚታሰበው፣ ግን አሁን ባለው 1.1 አካባቢ ነው ተብሏል።
“በዚህ ዓይነት ከቀጠለ ዓለም አትቀጥልም፤ ህዝብ እንዲቀጥል የሰው ልጅ መውለድ አለበት አለበት " ስትል ቤዛዊት አስረድታለች፡፡
ጥናቱ እንደሚያሳየው በተለይ ባደጉት አገራት ያሉ ወጣቶች ልጅ መውለድ አይፈልጉም። ቢወልዱም አንድ ነው። በአፍሪካ በተለይም በማዕከላዊ እና ደቡባዊ የአፍሪካ አገሮች ግን ቁጥሩ ከፍ ይላል፡፡
በምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ አገሮች ያሉ ወጣቶች ወደ 4 ልጅ ነው በአማካኝ መውለድ የሚፈልጉት፣ በስታቲስቲክስ አሁን ላይ ያለው 2 ነው በአማካኝ ሲታይ። አሊያም ደግሞ 2 ልጅ ነው መውለድ የሚፈልጉት፣ ግን በአማካኝ 1 ልጅ ነው እየወለዱ ያሉት" ተብሏል።
በዓለም ላይ ወጣቶች ትዳር ሲመሠርቱ፣ ሁለት እና ከዚያ በላይ ልጅ ለመውለድ የማይፈልጉት በኢኮኖሚ፣ በሰላም እና ደህንነት ችግሮች ምክንያት መሆኑን በUNFPA የሥነ ሕዝብ እና ልማት ፕሮግራም ተንታኝ የሆኑት ወይዘሮ ገዙ ብርሃኑ ነግረውናል።
የዓለም የሥነ ሕዝብ ቀን ዛሬ በአዲስ አበባ ሲከበር የተገኙት የፕላን እና ልማት ሚኒስትሯ ዶ/ር ፍጹም አሰፋ፣ ኢትዮጵያ ባለፉት 30 ዓመታት ስትጠቀምበት የቆየችውን የሕዝብ ቁጥር ፖሊሲ አሁን ያለውን ነባራዊ ሁኔታ በሚመጥን መልኩ ለማሻሻል እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል።
የወጣቶች ሕይወት እንዲሻሻል የኢትዮጵያ መንግሥት በርካታ ሥራዎችን እየሠራ ነው ያሉት ሚኒስትር ፍጹም፣ በግብርና፣ በአምራች፣ በማዕድን እንዲሁም በICT ዘርፎች እንዲሳተፉ እና የሥራ ዕድል እንዲፈጠር ለማድረግ እየተሠራ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
ንጋቱ ሙሉ
_edited.jpg)



Comments