የነሐሴ 8 2018 የውጪ ሀገር ወሬዎች
- 4 hours ago
- 2 min read
የተባበሩት አረብ ኢሚሬትስ በሆርሙዝ ወሽመጥ በሁለት መርከቦቼ ላይ ጥቃት ሰንዝራለች ያለቻትን ኢራንን በብርቱ ኮነነቻት ተባለ፡፡
ኢራን በነዳጅ ጫኝ መርከቦቻችን ላይ ጥቃት ሰንዝራለች ሲል ከበድ ያለ ተቃውሞውን ያሰማው የኢሚሬትስ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት እንደሆነ አልጀዚራ እና AFP ፅፈዋል፡፡
ያም ሆኖ የኢሚሬትስ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት በመርከቦቻችንም ሆነ በባህረኞቻቸው ላይ የደረሰ አንዳችም ጉዳት የለም ማለቱ ተሰምቷል፡፡
ኢሚሬትስ በሆርሙዝ መሰል ጥቃት ተሰንዝሮብኛል ስትል ሳምንት ባልሞላው ጊዜ የአሁኑ 2ኛዋ ነው ተብሏል፡፡
ባለፈው ሳምንት ቅዳሜም ኢሚሬትስ በሆርሙዝ ወሽመጥ በሌላ ነዳጅ ጫኝ መርከቤ ላይ ጥቃት ተሰንዝሮባታል ብላ እንደነበር መረጃው አስታውሷል፡፡
ኢራን ትዕዛዜን በሚተላለፉ መርከቦች ላይ እርምጃ እወስዳለሁ በሚለው አቋሟ እንደገፋችበት ይነገራል፡፡
ስለ አዲሱ የኢሚሬትስ ክስ ግን ከኢራን በኩል እንዲህም ነው ፤ እንዲያም ነው የተባለ ነገር የለም፡፡
የደቡብ አፍሪካ መንግስት የብዙ የአፍሪካ አገሮችን ስደተኞች ወደየአገራቸው ለመለስኩበት የወጪ ማካካሻ ሊከፈለኝ ይገባል አለ፡፡
የደቡብ አፍሪካ መንግስት ጥያቄ የተሰማው 80 ሺህ አፍሪካውያን ስደተኞችን ወደየአገሮቻቸው እንዲመለሱ ማድረጉን ተከትሎ እንደሆነ አፍሪካ ኒውስ ፅፏል፡፡
በደቡብ አፍሪካ ስደተኛ ጠል ወገኖች በተለይም ሰነድ አልባ ስደተኞች ተጠራርገው እንዲወጡ ግፊታቸውን እያበረከቱ ነው፡፡
ነገሩ ከጥያቄም አልፎ ወደ ጥላቻ ጥቃት ከተሸጋገረ ወራትን አስቆጥሯል፡፡
ለነፍሳቸው የፈሩ ስደተኞች በጊዜያዊ መጠለያዎች ለመቆየት ተገድደዋል፡፡
ጋና ቀደም ሲል ዜጎቿ በጥላቻ ጥቃቱ ፍራቻ በደቡብ አፍሪካ ትተውት ለመጡት ሐብት እና ንብረት የካሣ ጥያቄ አቅርባ ነበር፡፡
አሁን የደቡብ አፍሪካ መንግስት ስደተኞቹን ወደየገሮቻቸው ለመለስኩበት የወጪ ማካካሻ ያሻኛል ማለቱ ተሰምቷል
በኢንዶኔዥያ በወርቅ ማዕድን ስፍራ መደርመስ በጥቂቱ የ5 ሰዎች ሕይወት አለፈ ተባለ፡፡
መደርመሱ ያጋጠመው በመሬት መንሸራተት እንደሆነ አናዶሉ ፅፏል፡፡
የማዕድን ስፍራ መደርመስ አደጋው የደረሰው ጎሮንታሎ በተባለው ግዛት መሆኑ ታውቋል፡፡
በስፍራው የነበሩ ማዕድን አውጭዎች በህገ ወጥ ሁኔታ ሲሰሩ የነበሩ ናቸው ተብሏል፡፡
አደጋው የደረሰው በማዕድን ስፍራው አቅራቢያ ያለ ጋራ በመናዱ እንደሆነ ተጠቅሷል፡፡
በአደጋው ሕይወታቸው ማለፉ ከተረጋገጠው በተጨማሪ ሌሎችም በናዳው ስር የተቀበሩ ሳይኖሩ አልቀረም ተብሎ ተሰግቷል፡፡
የነፍስ አድን ባልደረቦች የተቀበሩትን ለማትረፍ እየጣሩ ነው ተብሏል፡፡
አንድ ሩሲያዊ የጦር መኮንን በክራይሚያ ልሳነ ምድር በቦምብ ጥቃት ተገደሉ ተባለ፡፡
የጦር መኮንኑ ማዕረጋቸው ባይጠቀስም ሮበርት ሻጌየቭ እንደሚባሉ በበርካታ የማህበራዊ ትስስር ገጾች መስፈሩን ሬውተርስ ፅፏል፡፡
የሩሲያ ሹሞች ለጦር መኮንን ግድያ ከዩክሬይን ራስ አንወርድም ማለታቸው ተሰምቷል፡፡
በጥቃት አድራሽነት የተጠረጠረች ሴት መያዟ ታውቋል፡፡
በሩሲያው የጦር መኮንን ላይ ስለተፈፀመው ግድያ ከዩክሬይን በኩል የተሰጠ አስተያየት የለም፡፡
የተገደሉት የሩሲያ የጦር መኮንን በቀደመው ጊዜ የዩክሬይን ባህር ሀይል ባልደረባ ነበሩ ተብሏል፡፡
ሩሲያ የክራይሚያ ልሳነ ምድርን ወደ ራሷ ግዛት የጠቀለለችው ከ12 አመታት በፊት እንደነበር መረጃው አስታውሷል፡፡
በሱዳን የRSF ፈጥኖ ደራሽ ሀይል በብሉ ናይል ግዛት ድል ቀንቶኛል አለ፡፡
ፈጥኖ ደራሽ ሀይሉ በብሉ ናይል ግዛት የምትገኘውን የጊዛን ከተማ ሙሉ በሙሉ ተቆጣጥረናታል ማለቱን አፍሪካ ኒውስ ፅፏል፡፡
በውጊያው SPLM- ኖርዝ የተሰኘው ታጣቂ ቡድንም ከRSF ጋር በተባባሪነት ታጣቂዎቹን በውጊያው አሰልፎ ነበር ተብሏል፡፡
ፈጥኖ ደራሽ ሀይሉ የጊዘን ከተማ ሙሉ በሙሉ በእጃችን አስገብተናታል ቢልም የሱዳን መንግስት ጦር በፊናው በከተማዋ ውጊያው ቀጥሏል ማለቱ ተሰምቷል፡፡
በሱዳን መንግስት ጦር እና በRSF ፈጥኖ ደራሽ ሀይል መካከል ጦርነቱ ከተቀሰቀሰ ከ3 አመታት በላይ ሆኖታል፡፡
የጦርነቱ አድማስ እየሰፋ መምጣቱ ይነገራል፡፡
የኔነህ ከበደ
_edited.jpg)


Comments