የነሐሴ 7 2018 የውጪ ሀገር ወሬዎች
- 2 hours ago
- 2 min read
ዩጋንዳ ከአውሮፓ የሚባረሩ የ3ኛ አገር ስደተኞችን ልትቀበል ነው ተባለ፡፡
ዩጋንዳ ከአውሮፓ ተባራሪዎቹን ተቀብላ ለማስተናገድ መዘጋጀቷን ካቲሜሪኒ የተሰኘ የግሪክ ጋዜጣ መዘገቡን አናዶሉ ፅፏል፡፡
ጋዜጣው ዘገባውን ያሰራጨው ዲፕሎማሲያዊ ምንጮችን በዋቢነት በመጥቀስ እንደሆነ ታውቋል፡፡
የሐሳቡ ቀዳሚ አፍላቂዎች ጀርመን ፣ ኦስትሪያ ፣ ዘ ኔዘርላንድስ እና እና ግሪክ መሆናቸው ተጠቅሷል፡፡
ዩጋንዳ በውጥኑ ቀዳሚ ስራ ላይ ማዋያ 10 ሺህ የ3ኛ አገር ከአውሮፓ ተባራሪ ጥገኝነት ፈላጊዎችን ተቀብላ ታስተናግዳለች ተብሏል፡፡
የአሜሪካው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ አስተዳደር ሰነድ አልባዎች ናቸው የተባሉ የ3ኛ አገራት ጥገኝነት ፈላጊዎችን ወደተለያዩ የአፍሪካ አገሮች እያባረረ መሆኑ ይታወቃል፡፡
ዩጋንዳ ከአውሮፓ ተባራሪዎቹን ጥገኝት ፈላጊዎች ልትቀበል ነው ስለመባሉ ከአገሪቱ ሹሞች በኩል የተሰማ አስተያየት የለም፡፡
የአለም የጤና ድርጅት የበላይ ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም በአሁኑ ወቅት በኮንጎ ኪንሻሣ በመዛመት ላይ የሚገኘው የኢቦላ ወረርሽኝ እስካሁን ካጋጠሙት ወረርሽኞች በሙሉ የከፋው ሊሆን ይችላል አሉ፡፡
ዶክተር ቴድሮስ የኮንጎው ኢቦላ እስካሁን ካጋጠሙት ወረርሽኞች ሁሉ የከፋው ይሆናል ያሉት ፈጣን ተዛማችነቱን በመጥቀስ እንደሆነ አናዶሉ ፅፏል፡፡
የኮንጎው ኢቦላ መቀስቀሱ ከተነገረ 3 ወራትን ሊደፍን ነው፡፡
በኢቦላ የተያዙ ሕሙማን ብዛት 4 ሺህ 450 ደርሷል፡፡
ወረርሽኙ የገደላቸው ሰዎች ብዛት ከ2 ሺህ መብለጡ ታውቋል፡፡
በታሪክ እጅግ ከባዱ ነው ሲባል የቆየው ከ10 አመታት በፊት በምዕራብ አፍሪካ ጊኒን ፣ ላይቤሪያን እና ሴራሊዮንን ከ2 አመታት በላይ የፈተነው የኢቦላ ወረርሽኝ ነው፡፡
የዚያን ጊዜው ወረርሽኝ የከሰመው ከ11 ሺህ በላይ ሰዎችን ከገደለ በኋላ እንደነበር መረጃው አስታውሷል፡፡
ገና በመጀመሪያ ደረጃ ሙከራ ላይ ከሚገኙ 2 ክትባቶች በስተቀር የኮንጎው የቡንዲቡጉዮ የኢቦላ ቫይረስ ምንም ዓይነት የፈውስ መድሐኒትም ሆነ የመከላከያ ክትባት እንደሌለው ይነገራል፡፡
የኢራቁ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓሊ አል ዛይዲ አገራቸው ጎረቤት አገሮችን ለማጥቃት የድብደባ መንደርደሪያ እንድትሆን አትፈቅድም አሉ፡፡
አል ዛይዲ የኢራቅ የምድርም ሆነ የአየር ክልል በጭራሽ የሌሎች ሀይሎች የጥቃት መንደርደሪያ አይሆንም ማለታቸውን የአገሪቱን ይፋዊ ምንጮች በመጥቀስ አልጀዚራ ፅፏል፡፡
የኢራቁ ጠቅላይ ሚኒስቴር ኢራቅን የጥቃት መደርደሪያ ያደርጋሉ ያሏቸውን አገሮች በስም ለይተው አልጠቀሱም፡፡
በቀጠናው በአሁኑ ወቅት አሜሪካ እና ኢራን ባልተቋረጠ የጦር ፍጥጫ ላይ መሆናቸው ይታወቃል፡፡
አል ዛይዲ ኢራቅ የአየር መከላከያ ሥርዓቷን ይበልጥ እንደምታጠናክር ተናግረዋል፡፡
የአየር ክልላችን እንዲጣስ በጭራሽ አንፈቅድም ማለታቸው ተሰምቷል፡፡
ኢራቅ የኢራን ወሰንተኛ አገር ነች፡፡
የኢራን ብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤተት አዲሱ ሰብሳቢ ሞኸሰን ሬዛኢ ለጦርነቱ መቆም አገራቸው ያቀረበችው ጥያቄዎች ተገቢውን ምላሽ እስኪያገኙ ድረስ ከአቋሟ ፍንከች አትልም አሉ፡፡
ኢራን ቀደም ሲል ጦርነቱ ሙሉ በሙሉ እንዲያበቃ እና የአሜሪካ የባህር ከበባ እንዲቆም ጠይቃለች፡፡
ከዚህም በተጨማሪ በየውጭ አገራቱ ተይዞባት የሚገኝ ገንዘብ በሙሉ እንዲመለስላት ጥያቄ ማቅረቧን አልጀዚራ አስታውሷል፡፡
ኢራን ጥያቄዎቿ እስኪሟሉ ድረስ የሆርሙዝ የባህር መተላለፊያ ወሽመጥን ዝግ አድርጋ ትቆያለች ብለዋል ፈዛኢ፡፡
ከሬዛኢ የማህበራዊ ትስስር መልዕክት አስቀድሞ የአሜሪካው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ ወሽመጡን የአሜሪካ ጦር ሙሉ በሙሉ እንደተቆጣጠረው ተናግረው ነበር፡፡
ቀደም ሲል ኢራን እና አሜሪካ ለጦርነቱ ማብቂያ የመግባቢያ ስምምነት ከተፈራረሙ ወዲህ የሆርሙዝ ወሽመጥ እልህ እያጋባቸው ነው፡፡
የኔነህ ከበደ
_edited.jpg)


Comments