top of page

ሚያዝያ 22፣2016 - ወጣት ስራ ፈጣሪዎችን ለማገዝ በቻይና ቢሮ ከፍቼ በብርቱ እየሰራሁ ነው ሲል የኢትዮጵያ ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ማህበር ተናገረ

ከ2 ሳምንት በኋላ 35 የቻይና ኢንተርፕራይዞች አዲስ አበባ ይመጣሉ ተብሏል


ወጣት ኢትዮጰያዊያን ስራ ፈጣሪዎችን በተለያየ መንገድ ለማገዝ በቻይና ቢሮ ከፍቼ በብርቱ እየሰራሁ ነው ሲል የኢትዮጵያ ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ማህበር ተናገረ፡፡


የዚህ ቢሮ በቻይና መከፈት፤ ለወጣት ኢትዮጵያዊያን ስራ ፈጣዎች ከተለያዩ የዓለም ሀገራት ጋር የገበያ ትስስር እንዲኖራቸው ያደርጋል ተብሏል፡፡


በተለይም ቻይና ካፍሪካ ሀገራት ጋር በምታደርገው የንግድ እና የኢንቨስትመንት ግንኙነት(China-Africa trade and investment promotion) ላይ ኢትዮጵያዊያን ስራ ፈጣሪዎች ግንዛቤ ኖሯቸው በንቃት እንዲሳተፉ ያግዛቸዋልም ተብሏል፡፡


በቻይና ቢሮ መክፈት ያሰፈለገውም ቻይና በዘርፉ የምታደርገው እንቅስቃሴ ሰፊ በመሆኑ እንደሆነ የኢትዮጵያ ስራ ፈጣሪ ወጣቶች ማህበር ፕሬዚደንት ሳሚያ አብዱልቃድር ነግረውናል፡፡

በውጭ ሀገራትና በሀገር ቤት በቢዝነስ ኢንቨስትመንት የመሳተፍ እድል ማግኘት፣ የገበያ ድርሻ፣ የቴክኖሎጂ እና ሌሎች ልምዶችን መቅሰም፤ ወጣት ስራ ፈጣሪዎቹ ይጠቀሙባቸዋል ተብለው ከተጠቀሱት መካከል ናቸው፡፡


በሌላ በኩል፤ ከ2 ሳምንት በኋላ 35 የቻይና ኢንተርፕራይዞች አዲስ አበባ ይመጣሉ ተብሏል፡፡


እነዚህ እንተርፕራይዞች ከማህበሩ እና ከአጋር አካላት ጋር ውይይት ለማድረግ ውጥን መያዙንም የማህበሩ ፕሬዚደንት ሳሚያ አብዱልቃድር አውርተውናል፡፡


ከዚህ በተጨማሪም ማህበሩ በየጊዜው ይፋ የማደርጋቸው ሌሎች ስራዎችም እየሰራሁ ነው ብሏል፡፡


ከማስተር ካርድ ፋውንዴሽን(VISA) ጋር እየሰራሁት ያለሁትም ከነዚህ ውስጥ ተቃሽ ነው ሲል ማህበሩ ለሸገር አስረድቷል፡፡



ማንያዘዋል ጌታሁን ያሰናዳውን በማርታ በቀለ


የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…





bottom of page