top of page

መጋቢት 25፣2016 - ግንባታዎች  ከዋና ከመንገድ በ10 ሜትር  ርቀት ሆነው እንደሚገነቡ የከተማዋ ካቢኔ ወሰነ

በአዲስ አበባ ከዚህ በኋላ የሚገነቡ ማንኛውም ግንባታዎች  ከዋና ከመንገድ በ10 ሜትር  ርቀት ሆነው እንደሚገቡ የከተማዋ ካቢኔ ወሰነ።


ከዚህ በተጨማሪም ከንዑስ ዋና መንገድ 5 ሜትር ርቀት፤ ሰብሳቢ መንገድ ደግሞ 3 ሜትር ርቀት በተጨማሪም የውስጥ ለውስጥ መንገድ 2 ሜትር ርቀት  መጠበቅ እንዳለባቸው ካቢኔው ተወያይቶ ውሳኔ አሳልፏል።


ይህ ውሳኔ የላለፈው የከተማዋን ስታንዳርድ እና መዋቅራዊ ፕላን ለማስጠበቅ እንዲሁም መልሶ ማፍረስ እንዳይገጥም ፤ ግንባታዎች ከመንገድ ያላቸው ርቀት ከዚህ በኋላ ወጥነት ያለው የከተማ አሰራር አንዲኖር በማሰብ ነው ተብሏል።


የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ 3ኛ ዓመት 11ኛ መደበኛ ስብሰባ በሶስት ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ ማሳለፉን የከንቲባ ቢሮ ያወጣው መግለጫ ተናግሯል።


የከተማዋን የተሽከርካሪ አስተዳደር ህግ እና ሥርዓት ለማስከበር የከተማ አስተዳደሩ ባወጣው የተሽከርካሪ ማቆሚያ አገልግሎት አሰጣጥ ረቂቅ ደንብን ለአሰራር በሚያመች መልኩ ሀሳብ ተሰጥቶበት ደንቡ ፀድቋል ተብሏል።


የነገዋ የሴቶች ተሀድሶ እና ክህሎት ማበልፀጊያ ማዕከል ማቋቋሚያ ደንብ ማዕከሉን በተለይም ለጎዳና ህይወት ፤ ለፆታዊ ጥቃት ሰለባ እና ለወሲብ ንግድ ተጋላጭ ለሆኑ ሴቶች ፣ መጠለያ፣ ማገገሚያ እና የተመሰቃቀለ ህይወታቸውን እንደገና ለማደስ የሚያስችል የሙያ እና ክህሎት ሥልጠናዎች የሚያገኙበትን እና በዘላቂነት እንዲቋቋሙ የሚያግዝ አቅም ያለዉ ማዕከል እንዲሆን ለማስቻል በሚያግዘው ማቋቋሚያ ደንብ ላይ ካቢኔው ተወያይቶ አጽድቋል ተብሏል።


ንጋቱ ሙሉ


የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…





ShegerFM: @ShegerFMRadio102_1

bottom of page