ሐምሌ 2 2017 - የውጪ ሀገር ወሬዎች
- sheger1021fm
- Jul 9
- 2 min read
ደቡብ ሱዳን ነፃነቷን ካገኘች ዛሬ 14ኛ ዓመቷን ብታስቆጥርም ምንም ዓይነት የነፃነት በዓል አታከብርም ተባለ፡፡
አገሪቱ በአሁኑ ወቅት ከፍተኛ ምጣኔ ሐብታዊ ችግር እግር ከወረች እንደተጠፈረች ሬዲዮ ታማዙጅ ፅፏል፡፡
በዚያ ላይ አሁንም ድረስ ከፀጥታ መደፍረስ እንዳልተላቀቀች ተጠቅሷል፡፡

ደቡብ ሱዳን ወደ ታላቅ የእርስ በርስ ጦርነት የገባችው ገና የ3ኛ ዓመት የነፃነት በዓሏን ለማክበር ሳትታደል ነበር፡፡
የእርስ በርስ ጦርነቱ ቢቆምም አሁንም ድረስ ከጦርነቱ የዞረ ድምር እንዳልወጣች ይነገራል፡፡
ፖለቲካዊ መረጋጋትም የላትም፡፡
የእስራኤል መንግስት የጋዛ ሰርጥ ፍልስጤማውያንን በሙሉ በራፋህ ሊያሰባስባቸው ነው፡፡
የእስራኤሉ የመከላከያ ሚኒስትር እስራኤል ካትዝ የአገሪቱ ጦር ፍልስጤማውያንን በራፋህ በሚሰናዳ የመጠለያ ጣቢያ እንዲጠቃለሉ የሚያስችል እቅድ እንዲያቀርብ ማዘዛቸውን እንደተናገሩ ቢቢሲ ፅፏል፡፡
በመጀመሪያ 600 ሺህ ፍልስጤማውያን ወደመጠለያው እንዲገቡ ይደረጋል ተብሏል፡፡
በተከታታይም ከ2 ሚሊዮን በላይ የጋዛ ፍልስጤማውያን በሙሉ በመጠለያው እንደሚሰባሰቡ ታውቋል፡፡
ወደ መጠለያው የሚገቡ ፍልስጤማውያን ከዚያ መውጣት በፍጹም እንደማይፈቀድላቸው ተጠቅሷል፡፡
የአሜሪካው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ የጋዛ ፍልስጤማውያንን በአቅራቢያው አገሮች በማስፈር ሰርጡን የቱሪስቶች መናኸሪያ አድርገዋለሁ የሚል ውጥናቸውን አሁንም አልተውትም፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጋዛ ፍልስጤማውያንን በግዴታ ማፈናቀሉ በግላጭ አለም አቀፍ ሕግን የሚጥስ ተግባር ነው ሲል መቃወሙን መረጃው አስታውሷል፡፡
በፈረንሳይዋ 2ኛ ታላቅ ከተማ ማርሴይ አቅራቢያ ከፍተኛ የሰደድ እሳት እየተዛመተ ነው ተባለ፡፡
የሰደድ እሳቱ በመቶዎች የሚቆጠሩ ቤቶችን እንዳወደመ ዘጋርዲያን ፅፏል፡፡
በፍጥነትም ከስፍራ ስፍራ በመዛመት ላይ ነው ተብሏል፡፡
የሰደድ እሳቱ ከሚያሰጋቸው ስፍራዎች በብዙ መቶዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን ማስወጣት እንደተቻለ ታውቋል፡፡
ከባዱ ጭስ ያስከተለው የእይታ መጋረድ የማርሴይ አለም አቀፍ ኤርፖርት ሁሉንም ገቢ እና ወጪ በረራዎችን እንዲሰርዝ አስገድዶታል፡፡
ብዙዎቹ የባቡር መስመሮች አገልግሎት እንዲያቋርጥ አድርጓል ተብሏል፡፡
የማርሴዩ አቅራቢያ የሰደድ እሳት የአውሮፓው የሙቀት ማዕበል ውጤት መሆኑ እየተጠቀሰ ነው፡፡
የሰደድ እሳቱ በ350 ሔክታር መሬት ላይ ያጋጠመውን ሁሉ እያወደመ ነው ተብሏል፡፡
የሩሲያው ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አሌክሳንደር ጉርሽኮ የሰሜን አትላንቲክ የጦር ቃልኪዳርን ድርጅት /ኔቶ/ ከሩሲያ ጋር ወደ ቀጥተኛ የጦር ግጭት ለመግባት እየተሰናዳ ነው አሉ፡፡
ጉርሽኮ በአውሮፓ ህብረትም ላይ ተመሳሳይ ክስ ማቅረባቸውን አናዶሉ ፅፏል፡፡
ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ውጥረቱ እጅግ አስጊ ወደሆነ ደረጃ እየተሸጋገረ መሆኑን ዱማ ለተሰኘው የሩሲያ ፓርላማ የታችኛው ምክር ቤት ተናግረዋል፡፡
የአውሮፓ የፀጥታ እና የትብብር ድርጅት (OSCE) ውጥረቱን ለማርገብ የሚጠበቅበትን አላደረገም ሲሉ ነቅፈዋል ጉርሽኮ፡፡
የዩክሬይኑ ጦርነት ከተቀሰቀሰ ወዲህ በኔቶ እና በሩሲያ መካከል የጦር ፍጥጫው እየገዘፈ መምጣቱ ይነገራል፡፡
አሁን ደግሞ የሩሲያው ምክትል የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ኔቶ ለጦር እርምጃ እየተሰናዳ ነው ሲሉ መክሰሳቸው ተሰምቷል፡፡
የኔነህ ከበደ












I have used the Escort Service in Chanakyapuri forever, and I am always left happy and impressed with the service.- Kumar