የእስራኤል እና የሊባኖስ መንግስታት የ10 ቀናት የተኩስ አቁም ለማድረግ ተስማሙ ተባለ፡፡
- 18 minutes ago
- 2 min read
ሚያዝያ 9/2018 - ዓለም አቀፍ ወሬዎች
የእስራኤል እና የሊባኖስ መንግስታት የ10 ቀናት የተኩስ አቁም ለማድረግ ተስማሙ ተባለ፡፡
በሁለቱ አገሮች መካከል የተኩስ አቁም ለማድረግ ስምምነት መደረሱን የአሜሪካው ፕሬዘዳንት በትሩዝ ማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ላይ ባሰፈሩት ፅሁፍ ማብሰራቸውን TRT ዎርልድ ፅፏል፡፡
በኢራን ላይ የአሜሪካ እና የእስራኤል የጦር ድብደባ በተጀመረ ሰሞን ወዲያው የሊባኖሱ ጦርነት መፈንዳቱ ይታወቃል፡፡
የእስራኤል የጦር ሹሞች ወደ ጦርነቱ የገነባው የሊባኖሱ ሺአ ታጣቂ ቡድን ወደ እስራኤል ሮኬቶችን በመተኮሱ ነው ባዮች ናቸው፡፡
ወደ ሊባኖስ ደቡባዊ ክፍል የዘለቀው የእስራኤል ጦር ከትናንት ምሽት 3 ሰዓት አንስቶ የተኩስ አቁም እንዲያደርግ መታዘዙ ተሰምቷል፡፡
ኢራንም በሊባኖስ ጭምር የተኩስ አቁም እንዲደረግ ስትጎተጉት ሰንብታለች፡፡
በተኩስ አቁም ድርድሩ ሔዝቦላህ እንዳልተሳተፈ መረጃው አስታውሷል፡፡
ይሁንና ታጣቂ ቡድኑ በተኩስ አቁም ስምምነቱ እንደሚገዛ ፍንጭ መስጠቱ ተሰምቷል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት እና የአውሮፓ ህብረት በየፊናቸው በእስራኤል እና በሊባኖስ መካከል ለ10 ቀናት የሚዘልቅ የተኩስ አቁም መደረሱን መልካም እርምጃ ነው አሉት፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ በእስራኤል እና በሊባኖስ መካከል ጊዜያዊ የተኩስ አቁም መደረሱ በእጅ አስደስቶኛል ማለታቸውን አናዶሉ ፅፏል፡፡
ከእንግዲህም ዋነኛ ትኩረት ሊሆን የሚገባው የተኩስ አቁሙን ወደ ዘላቂ ሰላም ማሸጋገሩ ሊሆን ይገባል ማለታቸው ተሰምቷል፡፡
የአውሮፓ ኮሚሽን ፕሬዘዳንትም ኡሩስላ ቮን ዴር ሌይን ተመሳሳይ ይዘት ያለው መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡
የተኩስ አቁሙ ጊዜያዊ እፎይታ እንደሚሰጥ የጠቀሱት የአውሮፓ ህብረት የበላይዋ ወደ ዘላቂ ሰላምም እንዲሸጋገር ጠይቀዋል፡፡
የሊባኖስ የግዛት አንድነት እና ሉዓላዊነት ሊከበር ይገባል ማለታቸውን መረጃው አስታውሷል፡፡
በሱዳን ምስራቃዊ ክፍል ባጋጠመ የማዕድን ስፍራ መደርመስ አደጋ የ5 ሰዎች ሕይወት አለፈ ተባለ፡፡
በማእድን ስፍራው መደርመስ አደጋ መሞታቸው ከተረጋገጠው በተጨማሪ 25 ሰዎች በጉድጓድ ውስጥ መፈናፈኛ ማጣታቸውን አናዶሉ ፅፏል፡፡
በጉድጓድ ውስጥ የተቀበሩትን ለማውጣት የነፍስ አድን ጥረቱ መቀጠሉ ታውቋል፡፡
በአደጋው አካላዊ ጉዳት አጋጥሟቸው በሕይወት የተረፉ በርካታ ሰዎች ወደ ሕክምና ተቋማት ተወስደዋል ተብሏል፡፡
በሱዳን የማዕድን ስፍራዎች መደርመስ አደጋ እንደሚደጋገም ይነገራል፡፡
ከ3 ወራት በፊትም በደቡብ ኮርዶፋን ግዛት በአንድ የወርቅ ማዕድን ማውጫ ስፍራ ባጋጠመ የመደርመስ አደጋ የ6 ሰዎች ሕይወት ሲያልፍ በ12ቱ ላይ ደግሞ አካላዊ ጉዳት መድረሱን መረጃው አስታውሷል፡፡
የሶማሊያ መንግስት ጦር በጁባላንድ ባካሄድኩ ዘመቻ 27 የአልሸባብ ፅንፈኛ ቡድን ታጣቂዎችን ገደልኩ አለ፡፡
ጦሩ በዘመቻው በአፍሪካ ህብረት ሰራዊት መደገፉን TRT አፍሪካ ፅፏል፡፡
ዘመቻው በአየር ድብደባም የታገዘ ነበር ተብሏል፡፡
በዘመቻው የፅንፈኛው ቡድን የነበሩ በርካታ የጦር መሳሪያዎች እና ፈንጂዎች መማረካቸው ተጠቅሷል፡፡
በውጊያው በሶማሊያ ጦር ባልደረቦች ላይ ስለደረሰ ጉዳት የተጠቀሰ ነገር የለም፡፡
የሶማሊያ መንግስት ጦር ከፅንፈኛው ቡድን ጋር ሲዋጋ በርካታ አመታትን አስቆጥሯል፡፡
የኔነህ ከበደ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
X :- https://x.com/shegerfm?s=2
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7

