የሐምሌ 17 2018 የውጪ ሀገር ወሬዎች
- 11 hours ago
- 2 min read
የብሪታንያ መንግስት በኬንያ ላካሂድ የነበረውን አመታዊ የጦር ልምምድን ትቼዋለሁ አለ፡፡
የብሪታንያ ሰራዊት አመታዊ የኬንያ የጦር ልምምዱን የተወው ከምስራቅ አፍሪካዊቱ አገር መንግስት ፈቃድ ባለማግኘቱ ነው መባሉን አፍሪካ ኒውስ ፅፏል፡፡
የብሪታንያ ጦር ከዚህ ቀደም በኬንያ በየአመቱ በመደበኛነት የጦር ልምምዱን ሲያደርግ መቆየቱን መረጃው አስታውሷል፡፡
የኬንያ መንግስት ለብሪታንያ አመታዊ የጦር ልምምድ ፈቃድ የነሳበት ምክንያት አልተጠቀሰም፡፡
የሚመለከታቸው ሹሞችም ከAFP ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ ከመስጠት ተቆጥበዋል ተብሏል፡፡
የብሪታንያ ጦር ይሄንኑ አመታዊ ወታደራዊ ልምምዱን በሌላ አፍሪካ አገር ያካሂዳል ተብሏል፡፡
የልምምዱ አስተናጋጅ የአፍሪካ አገር ማን እንደሆነች በስም አልተጠቀሰችም፡፡
የአሜሪካው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ በኢራን ላይ ከእስካሁኑ የከፋ ድብደባ እንፈፅምባታለን ሲሉ ዛቱ።
ትራምፕ የእስካሁኑ ድብደባችን ኢራንን ገና አላመማትም ማለታቸውን አልጀዚራ ፅፏል፡፡
አሜሪካ በኢራን ላይ ለ13ኛ ተከታታይ ሌሊቶች ድብደባ መፈፀሟ ተሰምቷል፡፡
በተለይም በኢራን ደቡባዊ ክፍል ከባባድ ፍንዳታዎች ሲሰሙ እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
የኢራኑ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አባስ አራግቺ አሜሪካ ለዚህ ሁሉ ዋጋዋን ታገኛለች ማለታቸው ተሰምቷል።
ትራምፕ ታግዶ የሚገኘው የኢራን ገንዘብ ጥቃት ለሚደርስባቸው መርከቦች ካሳነት ይውላል ማለታቸውን ደግሞ የፃፈው AFP ነው፡፡
ኢራን በሆርሙዝ ወሽመጥ በኩል ለማለፍ በሚሞክሩ መርከቦች ላይ ጥቃት እየሰነዘረች መሆኑ ይነገራል፡፡
ዘግይቶ ደግሞ የየመን ሁቲዎችም በቀይ ባህር ይሄንኑ መላ እየተከተሉ ነው ይባላል፡፡
የአሜሪካው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ በ60 ያህል አገሮች ላይ ከ10 እስከ 12 ነጥብ 5 በመቶ የቀረጥ ታሪፍ መጣላቸውን እወቁልኝ አሉ፡፡
ትራምፕ አዲሱን የቀረጥ ታሪፍ ስራ ላይ አውላለሁ ያሉት አገሮቹ የግዳጅ ስራን ሊያስቆሙ አልቻሉም በሚል ምክንያት እንደሆነ ቢቢሲ ፅፏል፡፡
አዲሱ የቀረጥ ታሪፍ ከተጣለባቸው መካከል ብሪታንያ ፣ ቻይና ፣ የአውሮፓ ህብረት ፣ ካናዳ ፣ ጃፓን እና ሕንድ ይገኙበታል ተብሏል፡፡
ቀደም ሲል የአሜሪካ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዘዳንቱ የአስቸኳይ ጊዜ ህግን ተንተርሰው ጥለውት የነበረውን የ10 በመቶ የቀረጥ ህገ ወጥ ነው ብሎት እንደነበር መረጃው አስታውሷል፡፡
አዲሱ የትራምፕ የቀረጥ ታሪፍ እርምጃ አለም አቀፋዊ የንግድ ጦርነት ሊቀሰቀስ እንደሚችል ተገምቷል፡፡
እንደሚባለው ትራምፕ ወደ አዲሱ የቀረጥ ታሪፍ እርምጃ የገቡት ቀደም ሲል በጠቅላይ ፍርድ ቤቱ የተሰጠባቸውም ትዕዛዝ ለማምለጥ ነው፡፡
ትራምፕ በ47ኛ ፕሬዘዳንትነት ወደ ዋይት ሐውስ ከተመለሱ ወዲህ የቀረጥ ታሪፍ ቁለላን የአስተዳደራቸው መለያ እንዳደረጉት መረጃው አስታውሷል፡፡
የአሜሪካው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ ሳውዲ አረቢያ ኒኩሊየርን ለሰላማዊ አገልግሎቶች እንድታውል በደረስነው ስምምነት ለውጥ ከሪያድ የምንጠብቀው ነገር አለ አሉ፡፡
ትራምፕ በትሩዝ ማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ባሰፈሩት ፅሁፍ በስምምነቱ ለውጥ ሳውዲ አረቢያ ከእስራኤል ጋር ይፋዊ ግንኙነት መመስረት ይኖርባታል ማለታቸውን አልጀዚራ ፅፏል፡፡
ሳውዲ አረቢያ ከአሜሪካ ጋር የደረሰችው ኒኩሊየር ነክ ስምምነት ከእስራኤል ጋር ይፋዊ ግንኙነት እንድትመሰርት የሚጠይቅ ነው ተብሏል፡፡
ሳውዲ አረቢያ በዚህ ጉዳይ የሰጠችው አስተያየት የለም፡፡
ቀደም ሲል ሳውዲ አረቢያ ከእስራኤል ጋር ይፋዊ ግንኙነት የመመስረቱን ጉዳይ የማጤነው የፍልስጤማዊና ነፃ አገር መመስረቱ ሳረጋግጥ ብቻ ነው ማለቷ ተጠቅሷል፡፡
ቀደም ሲል በአሜሪካ አግባቢነት የተባበሩት አረብ ኢሚሬትስ ፣ ባህሬን እና ሞሮኮ ከእስራኤል ጋር ይፋዊ ግንኙነት የመሰረቱ አገሮች ናቸው፡፡
አሜሪካ ሌሎችም የአረብ እና የሞስሊም አገራት የነኢሚሬትስን ፈለግ እንዲከተሉ ግፊት እያደረገች መሆኑ ይነገራል፡፡
የኔነህ ከበደ
_edited.jpg)

Comments