በተደጋጋሚ ተለዋጭ ቀጠሮ ሲሰጥበት የቆየው የእነ አቶ ክርስቲያን ታደለ መዝገብ የዋናው ክስ ብይን ዛሬም በድጋሚ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጠበት።
- 14 hours ago
- 2 min read
ሐምሌ 17 2018
በተደጋጋሚ ተለዋጭ ቀጠሮ ሲሰጥበት የቆየው የእነ አቶ ክርስቲያን ታደለ መዝገብ የዋናው ክስ ብይን ዛሬም በድጋሚ ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጠበት።
ተለዋጭ ቀጠሮው ለሚቀጥለው ዓመት ጥቅምት ወር ይሁን ብሏል ችሎቱ።
ተከሳሾቹ በበኩላቸው በተደጋጋሚ በሚሰጡ ቀጠሮዎች ምክንያት «ፍትህ እየተጓተተብን ነው» ሲሉ ለችሎቱ ቅሬታ አቅርበዋል።
በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው በማረሚያ ቤት የሚገኙት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባሎቹ አቶ ክርስቲያን ታደለ፣ አቶ ዮሐንስ ቧያለው እና ሌሎች ተከሳሾች የክስ ብይን ይሰጣል ተብሎ ተደጋጋሚ ቀጠሮዎችን ሲያስተናግድ ቆይቶ፤ ዛሬም በተመሳሳይ ለሚቀጥለው ዓመት ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል።
ከዚህ በፊት በነበረው ቀጠሮ «ተከሳሾቹ መከላከያ ማስረጃ ያቅርቡ ወይስ በነፃ ይሰናበቱ?» በሚለው ላይ ብይን ለመስጠት እንዲሁም የዶክተር ካሳ ተሻገርን እና የጋዜጠኛ ቴዎድሮስን ስልክ ሌላ ሰው እየተጠቀመበት በመሆኑ ከኢትዮ ቴሌኮም የሚሰጠውን ምላሽ ለመጠባበቅ ለዛሬ ሐምሌ 17 ቀን 2018 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቶ ነበር።
የዶክተር ካሳ ተሻገር እና የጋዜጠኛ ቴዎድሮስን ስልክ በተመለከተ ከኢትዮ ቴሌኮም የተላከው ምላሽ በችሎቱ በንባብ ተሰምቷል።
ኢትዮ ቴሌኮም በሰጠው ምላሽ «የሁለቱ ተከሳሾች ስልክ ቁጥሮች ከአገልግሎት ውጭ የሆኑበት ጊዜ ስላአበቃ፣ በቴሌኮሙ ደንብ መሰረት ቁጥሮቹ ለሌሎች ተጠቃሚዎች ተዘዋውረዋል» ብሏል።
ብይኑ ዛሬ ያልተነበበበትና ተለዋጭ ቀጠሮ የተሰጠበት ምክንያት ተከሳሾቹ በሙሉ በችሎት ባለመገኘታቸው እንደሆነ ፍርድ ቤቱ አሳውቋል።
ተከሳሾቹ በበኩላቸው «በተለያዩ ጥቃቅን ምክንያቶች ፍትህ እየተጓተተብን ነው። ያለ ምንም ውሳኔ ሦስት ዓመት ሙሉ መቆየቱ ተገቢ አይደለም» ሲሉ ቅሬታቸውን አቅርበዋል።
በተጨማሪም «ችሎቱ ብይኑን ያውቀዋል፤ ስለዚህ በተራዘመ ቀጠሮ ከሚተላለፍ ይልቅ በአጭር ቀን ተቀጥሮ ለምን ብይኑ አይነበብም?» ሲሉ ጠይቀዋል።
የችሎቱ ዳኞችም «በእርግጥ ችሎቱ ብያኔውን ቀድሞ ያውቀዋል። ነገር ግን አንድ በወንጀል የተከሰሰ ሰው እሱ ማረሚያ ቤት እያለ ባልተገኘበት ሁኔታ ብይን ሊነበብ አይችልም ብለዋል።
ተከሳሹ የቀረው እምቢተኛ ሆኖ ቢሆን ኖሮ ምናልባት ሊነበብ ይችል ነበር፤ ነገር ግን አንደኛ ተከሳሽ የተከበሩ አቶ ዮሐንስ ቧያለው "ታምሜአለሁ" ብለው በመቅረታቸው ምክንያት ችሎቱ ብይን መስጠት አይችልም» ሲሉ አስረድተዋል።
በዚህ መሰረት ታማሚው ተሽሏቸው ሲገኙ ብይኑ እንደሚነበብ ገልጸው፣ «የመከላከያ ማስረጃ ያቅርቡ ወይስ በነፃ ይሰናበቱ?» በሚለው ላይ ብይን ለመስጠት ለጥቅምት 06 ቀን 2019 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥተዋል።
ከነሐሴ 01 እስከ መስከረም 30 ባሉት ሁለት ወራት ፍርድ ቤቶች በከፊል ዝግ ሆነው እንደሚቆዩ ይታወቃል፡፡
ገዛ ጌታሁን
_edited.jpg)

Comments