የሐምሌ 16 2018 የውጪ ሀገር ወሬዎች
- 2 days ago
- 2 min read
በሊቢያ የተለያዩ የፖለቲካ ማህበራት አገሪቱ ወደ አንድነቷ እንድትመለስ ጥሪ አቀረቡ፡፡
የፖለቲካ ማህበራቱ በጋራ የህውደት ጥሪውን ያቀረቡት የሊቢያን የወደፊት እጣ ፈንታ በተመለከተ ምክክር ባደረጉበት ወቅት እንደሆነ TRT አፍሪካ ፅፏል፡፡
በሊቢያ የቀድሞው መሪ የኮሎኔል ሙአመር ጋዳፊ አስተዳደር ከ15 አመታት በፊት በትጥቅ አመፅ ከተወገደ በኋላ ብሔራዊ አንድነቷ ሊፀና አልቻለም፡፡
አገሪቱ በምስራቅ እና ምዕራብ እንደተከፋፈለች ነው፡፡
ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የሊቢያ የብሔራዊ አንድነት ጥሪ እየጎላ ነው፡፡
የፖለቲካ ማህበራቱ ሊቢያ ወደ ብሔራዊ አንድነቷ እንድትመለስ አጋዥ የሆነ ፕሬዘዳንታዊ እና የፓርላማ ምርጫ እንዲከናወንም ጥሪ ማቅረባቸውን መረጃው አስታውሷል፡፡
የየመን ሁቲዎች አንሳር አላህ ንቅናቄ በሁለት የሳውዲ አረቢያ የነዳጅ መጫኛ መርከቦች ላይ ጥቃት አድርሻለሁ አለ፡፡
ሁቲዎቹ ሁለቱን የሳውዲ አረቢያ ነዳጅ መጫኛ መርከቦች በክሩዝ እና በባሊስቲክ ሚሳየሎች መትተናል ማለታቸውን አልጀዚራ ፅፏል፡፡
የብሪታንያው የባህር ንግድ ተከታታይ አካልም በሁለት የሳውዲ አረቢያ የጭነት መርከቦች ላይ ጥቃት እንደተፈፀመባቸው አረጋግጧል ተብሏል፡፡
ጥቃቱ የተፈፀመው በቀይ ባህር መሆኑ ተጠቅሷል፡፡
በመርከቦቹ እና በባህረኞቻቸው ላይ የደረሰው ጉዳት በዝርዝር ባይታወቅም መርከቦቹ ከባድ ቃጠሎ እንደገጠማቸው ተሰምቷል፡፡
ሰሞኑን ሁቲዎቹ የሳውዲ አረቢያን ወደቦች እንከረቻችምባታለን ሲሉ ዝተው ነበር፡፡
ሳውዲ አረቢያ ሁቲዎቹ እንደ ሁዴይዳ ባሉ ወደቦች መርከቦችን እንዳያስጠጉ ስታደርግ መቆየቷ ለትውስታ ተነስቷል፡፡
የየመንን ሰሜናዊ ክፍል የሚያስተዳድሩት ሁቲዎቹ የኢራን የጦር እና የፖለቲካ ሸሪኮች መሆናቸው ይነገራል፡፡
በፈረንሳይ ባለፈው ወር ከሙቀት ማዕበል ጋር በተያያዘ የጤና እክል የ5 ሺህ 700 ሰዎች ሕይወት አልፏል ተባለ፡፡
የሞት መጠኑ ከዚህ ቀደም በሙቀት ወራት ሲያጋጥሙ ከነበሩት ሁሉ ከፍተኛው እንደሆነ አሶሼትድ ፕሬስ ፅፏል፡፡
ፈረንሳይ ከ23 ቀናት በፊት በተጠናቀቀው ወር በብዙ አካባቢዎች ከ40 ዲግሪ ሴሊሺየስ በላይ የሙቀት መጠን ማስመዝገቧ ተጠቅሷል፡፡
በፈረንሳይ ከ23 ቀናት በፊት በተጠናቀቀው ወር ከሙቀት ማዕበሉ ጋር የተያያዘው የሞት ምጣኔ ከፍ የማለቱ መረጃ የአገሪቱ የጤና ሹሞች ነው ተብሏል፡፡
ዘንድሮ ብዙዎቹ የአለማችን አገሮች በሙቀት ማዕበል እየተፈተኑ መሆኑን መረጃው አስታውሷል፡፡
የቡልጋሪያ ፓርላማ የአሜሪካ የጦር አውሮፕላኖች የቤዝሜር አየር ሀይል ሰፈርን እንዲገለገሉ በሚያስችል ጉዳይ ድምፅ ሊሰጥ ነው ተባለ፡፡
ቀደም ሲል አሜሪካ የቡልጋሪያውን የቤዝሜር አየር ሀይል ሰፈርን ለኢራኑ ውጊያ መንደርደሪያነት ለመገልገል ጥያቄ ማቅረቧን አረብ ኒውስ ፅፏል፡፡
የቤዝሜር አየር ሀይል ሰፈር በደቡባዊ ምስራቅ ቡልጋሪያ የሚገኝ ነው ተብሏል፡፡
እንደሚባለው አሜሪካ የአየር ሀይል ሰፈሩን መገልገል የፈለገችው በአየር ላይ ነዳጅ ለሚሞሉ የጦር አውሮፕላኖቿ መነሻ እና ማረፊያነት ነው፡፡
የቡልጋሪያው የመከላከያ ሚኒስትር የአየር ሀይል ሰፈራችንን የምንፈቅደው ለድጋፍ ሰጭዎቹ እንጂ ለተዋጊዎቹ አይደለም ማለታቸው ተሰምቷል፡፡
የኢራን የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ቡልጋሪያ የአሜሪካ ጥያቄ የወረራ ማጠናከሪያ መሆኑን ተረድታ ጥያቄውን ውድቅ እንድታደርገው ቀደም ብሎ ማስጠንቀቁን መረጃው አስታውሷል፡፡
የኔነህ ከበደ
_edited.jpg)

Comments