ከሳምንት በፊት ከናይጄርያ ኬቢ ግዛት አዳሪ ትምህርት ቤት ታግተው የተወሰዱ ሴት ተማሪዎች በሙሉ ተለቀቁ፡፡
- sheger1021fm
- 3 minutes ago
- 2 min read
ህዳር 17 2018 - የውጪ ሀገራት ወሬዎች
ከሳምንት በፊት ከናይጄርያ ኬቢ ግዛት አዳሪ ትምህርት ቤት ታግተው የተወሰዱ ሴት ተማሪዎች በሙሉ ተለቀቁ፡፡
በጊዜው 25 ሴት ተማሪዎች ታግተው እንደነበር ቢቢሲ አስታውሷል፡፡
አንዷ አስቀድሞ ከአጋቾቿ ማምለጧ ሲነገር ሰንብቷል፡፡
ታጋቾቹን ሴት ተማሪዎች ለማስለቀቅ የናይጀሪያ የፀጥታ ሀይሎች በፕሬዘዳንት ቦላ ቲኑቡ ትዕዛዝ በቅንጅት አሰሳ ላይ ተሰማርተው ነበር፡፡

ሴት ተማሪዎቹ ከእገታ ተለቀዋል ቢባልም በምን ዓይነት ሁኔታ እንደተለቀቁ የተብራራ ነገር የለም፡፡
ባለፈው ሳምንት አርብ ደግሞ ከኒጀር ግዛት የካቶሊክ ትምህርት ቤት ከ250 በላይ ተማሪዎች ታግተው መወሰዳቸውን መረጃው አስታውሷል፡፡
ከኒጀር ግዛት ታግተው የተወሰዱት ተማሪዎች ግን እንዳልተለቀቁ ተጠቅሷል፡፡
የብራዚሉ የቀድሞ ፕሬዘዳንት ጂየር ቦልሶናሮ ቀደም ሲል የተፈረደባቸውን የእስር ቅጣት ጊዜ በእስር ቤት ማሳለፍ ጀመሩ፡፡
ቦልሶናሮ ከ3 ዓመታት በፊት በምርጫ ከተሸነፉ በኋላ የአሁኑን የብራዚል ፕሬዘዳንት ሉላ ኢናሲዮ ዴ ሲልቫን መንግስት ለመገልበጥ እና ፕሬዘዳንቱንም ለማስገደል በመሞከር በፍርድ ቤት ጥፋተኛ ተብለው ከ27 አመታት በላይ የእስር ቅጣት የተፈረደባቸው ቀደም ብሎ ነው፡፡
ሆኖም ጉዳያቸው በይግባኝ እስኪታይ በቤት ውስጥ የቁም እስር እንዲውሉ ተደርገው እንደነበር አሶሼትድ ፕሬስ አስታውሷል፡፡
ቦልሶናሮ የቁም እስር ገደባቸውን በመተላለፋቸው ጉዳዩን የሚያዩት የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ዳኛ የቀድሞው ፕሬዘዳንት ወደ እስር ቤት እንዲገቡ ማዘዛቸው ተሰምቷል፡፡
በትዕዛዙ መሰረት ቦልሶናሮ እና በግልበጣ ሙከራው አባሪ ተባባሪዎቻቸው ነበሩ የተባሉ ፍርደኞች እስር ቤት መግባታቸው ታውቋል፡፡
የቦልሶናሮ ጠበቆች ግን በደንበኛቸው ጤና መጓደል የተነሳ የቁም እስረኝነታቸው እንዲቀጥል እንሟገታለን ማለታቸው በመረጃው ተጠቅሷል፡፡
በደቡብ ሱዳን የእርዳታ ምግብ ጭኖ ሲበር የነበሩ አውሮፕላን በመከስከሱ አሳፍሯቸው የነበሩ 3 ሰዎች በሙሉ ሞቱ፡፡
አውሮፕላኑ የተከሰከሰው በዩኒቲ ግዛት እንደሆነ ሬውተርስ ፅፏል፡፡
በምን ምክንያት እንደተከሰከሰ ለጊዜው የታወቀ ነገር የለም፡፡
ለክፉ እጣ የተዳረገው አውሮፕላን ሁለት ቶን የእርዳታ ምግብ ጭኖ ነበር ተብሏል፡፡
አውሮፕላኑ የተከሰከሰው ወደ ሊር አየር ማረፊያ በተቃረበበት አጋጣሚ መሆኑ ታውቋል፡፡
የእርዳታ አቅራቢው ድርጅት አውሮፕላኑን ናሪ ከተሰኘው የግል አየር መንገድ የተከራየው እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
አውሮፕላኑ ከመከስከሱ ውጭ ስለ ስሪቱ የተባለ ነገር የለም፡፡
የኔነህ ከበደ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
👇👇👇
🌐Website፡ https://www.shegerfm.com/
🎥YouTube https://tinyurl.com/37tux478
🟦Telegram https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📘Facebook፡ https://tinyurl.com/4tx8t8wm
💬WhatsApp ፡ https://tinyurl.com/ycxjmm3s








