በኢትዮጵያ ንፁህ መጠጥ ውሃ የሚያገኘው ህዝብ ቁጥር 81.2 ሚሊየን ደርሷል ተባለ።
- 6 hours ago
- 2 min read
መጋቢት 15/2018
በኢትዮጵያ ንፁህ መጠጥ ውሃ የሚያገኘው ህዝብ ቁጥር 81.2 ሚሊየን ደርሷል ተባለ።
ኢትዮጵያ ለጅቡቲ በቀን 100 ሺህ ሜትር ኪዩብ የመጠጥ ውሃን እያቀረበች መሆኑም ተነግሯል።
በቢሾፍቱ እየተካሄደ ባለው የውሃ ዲፕሎማሲና ኮሚኒኬሽን ጉባኤ ላይ የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ.ር) ሲናገሩ እንደሰማነው ንፁህ የመጠጥ ውሃ የሚያገኘው ህዝብ 81.2 ሚሊየን ደርሷል።
ግን ዛሬም ከመጠጥ ውሃ አቅርቦት ጋር በተገናኘ ብዙ ጥያቄ ይነሳል።
በሳምንት አንዴና ሁለቴ ነው የምናገኘው ከሚለው አንስቶ በየቦታው ከንፁህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ጋር በተገናኘ የሚነሳው ጥያቄ ብዙ ነው።
የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ሀብታሙ ኢተፋ(ዶ.ር) ይህ ጥያቄ በየጊዜው እንደሚነሳ እናውቃለን ይላሉ።
በውሃ እጥረት ምክንያት ሁሉም ሰው በግቢውና በቤቱ ጣራ ማጠራቀሚያ አስቀምጧል ያሉት ሚኒስትሩ ውሃ ሲለቀቅ ሁሉም ለማጠራቀም እንደሚሯሯጥ ተናግረዋል።

በዚህ ምክንያት ለአንድ አካባቢ ለረጅም ጊዜ ሊቆይ የሚችለው ውሃ ወደ ማጠራቀሚያ ይገባል ብለዋል።
ይህ ችግር በመላው ሀገሪቱ ያለ ነው ብለው፣ በዚህ መንገድ ከፍተኛ ውሃ በየቤቱ በማጠራቀሚያ እየተያዘ ውሃ ሳይጠፋ ከሳምንት ሳምንት እንዲቀጥል ለማድረግ እንቸገራለን ብለዋል።
በሌላ በኩል ኢትዮጵያ ከጎረቤት ሀገር ጋር ባላት የመሰረተ ልማት ትስስር ለበርካታ ዓመታት ንፁህ የመጠጥ ውሃን ለጅቡቲ ስታቀርብ እንደነበር አንስተው በአሁኑ ሰዓት በቀን የሚቀርበው የውሃ መጠን 100 ሺህ ሜትር ኪዩብ ደርሷል ብለዋል።
#የንፁህ_መጠጥ_ውሃ ፕሮጀክቱ በሁለቱ ሀገራት የውሃ ስምምነት መሰረት ከስምንት ዓመት ገደማ በፊት ከቻይና መንግስት በተገኘ ብድር ወደ ስራ መግባቱ የሚታወስ ነው።
የከርሰ ምድር ጉድጓዶችን በሶማሌ ክልል ሺንሌ በመቆፈር የመጠጥ ውሃው በሚሎ፣ሐረዋ፣አዲጋላ፣ለአስራት፣አይሻ፣ደወሌ አድርጎ 258 ኪሎ ሜትር ተጉዞ ጅቡቲ ይደርሳል።
ፕሮጀክቱ ከዚህ ቀደም ሲጀመር ውሃ ለመሳብ ነዳጅ የሚጠቀም ሲሆን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደ አሌክትሪክ መቀየሩ ተነግሯል።
ሲጀመር የነበረው በቀን የሚቀርበው የውሃ መጠንም ከ20 ሺህ ሜትር ኪዩብ፣በቀን ወደ 100 ሺህ ሜትር ኪዩብ ማደጉም ተነግሯል።
የሚኒስትሩ በሀገር ውስጥ ያለውን ፍላጎት ከማሟላት ስራ ባለፈ እንዲህ አይነቱ ትብብርም ለኢትዮጵያ በጣም ጠቃሚ ነው ብለዋል።
ቴዎድሮስ ወርቁ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
X :- https://x.com/shegerfm?s=2
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7





Comments