ሐምሌ 28 2017 - የውጪ ሀገራት ወሬዎች
- sheger1021fm
- Aug 4
- 2 min read
በየመን የባህር ዳርቻ ባጋጠመ የጀልባ ተገልብጦ መስጠም አደጋ ከ60 በላይ ስደተኞች ሕይወት አለፈ ተባለ፡፡
አደጋው የደረሰው በየመን አቢያን ግዛት አቅራቢያ እንደሆነ ቢቢሲ ፅፏል፡፡
12 ስደተኞችን ከአደጋው በሕይወት ማትረፍ እንደተቻለ ታውቋል፡፡
የየመን ሹሞች እስካሁን የ68 ስደተኞች አስከሬን ተገኝቷል ብለዋል፡፡

ለክፉ እጣ የተዳረገችው ጀልባ 150 ያህል ስደተኞችን አሳፍራ እንደነበር መረጃው አስታውሷል፡፡
በአደጋው የደረሱበት የጠፋም እንዳሉ ተጠቅሷል፡፡
በየመን የአለም አቀፉ የፍሰተኞች ድርጅት /IOM/ የየመን ተወካይ አብዛኞቹ የአደጋው ሰለባዎች ኢትዮጵያውያን እንደሆነ ግምታቸው ተናግረዋል፡፡
በሱዳን ዳርፉር ግዛት ኮሌራ በወረርሽኝ ደረጃ እየተዛመተ በመሆኑ የተባበሩት መንግስታት የህፃናት መርጃ ድርጅት /ዩኒሴፍ/ ከፍተኛ ስጋት ገብቶኛል አለ፡፡
በግዛቲቱ በኮሌራ የተያዙ ከ2 ሺህ በላይ ሰዎች እንደተገኙ ዩ ኤን ኒውስ ፅፏል፡፡
በበሽታው ከ80 ያላነሱ ሰዎች ሕይወት ማለፉ ተጠቅሷል፡፡
ሕፃናትም የወረርሽኙ ሰለባዎች ናቸው ተብሏል፡፡
የሱዳን መንግስት ጦር እና RSF የተሰኘው ፈጥኖ ደራሽ ሀይል ከ2 አመታት በላይ በውጊያ ላይ ናቸው፡፡
ዳርፉርም አንዷ የውጊያ አውድማቸው እንደሆነች መረጃው አስታውሷል፡፡
ጦርነቱ ያስከተለው መፈናቀል እንደ ወግ ላሉ ወረርሽኞች መዛመት ምክንያት እየሆነ መምጣቱ ይነገራል፡፡
ቻይና እና ሩሲያ የጋራ የጦር ልምምድ እያደረጉ ነው ተባለ፡፡
ሁለቱ አገሮች የጋራ የጦር ልምምዳቸውን የሚያካሂዱት በጃፓን ባህር እንደሆነ አልጀዚራ ፅፏል፡፡
ቻይና እና ሩሲያ ገደብ አልባ የሁለንተናዊ ትብብር ስምምነት የተፈራረሙት ከ3 አመታት በፊት ነው፡፡
ሁለቱ አገሮች በጃፓን ባህር የጀመሩት የጦር ልምምድ የትብብራቸው ማሳያ ተደርጎ እየተቆጠረ ነው፡፡
የጦር ልምምዱ በባህር ሀይል ላይ ያተኮረ ነው ተብሏል፡፡
ቻይና እና ሩሲያ ከብሪክስ ቀዳሚ መስራች አባሎች መካከል እንደሆኑ መረጃው አስታውሷል፡፡
በሩሲያ ሩቅ ምስራቅ ካምቻትካ ግዛት ከባድ እሳተ ገሞራ ፈነዳ፡፡
የካምቻትካው እሳተ ገሞራ ሲፈነዳ የአሁኑ ከ500 አመታት በኋላ የመጀመሪያው እንደሆነ ቢቢሲ ፅፏል፡፡
የእሳተ ገሞራ ፍንዳታው የደረሰው ከመኖሪያ አካባቢ ርቆ በመሆኑ በሰዎች ላይ ያደረሰው ጉዳት የለም ተብሏል፡፡
በካምቻትካ የእሳተ ገሞራ ፍንዳታው ያጋጠመው ሰሞኑን በዚያው የባህር ዳርቻ ከደረሰ ከባድ የመሬት ነውጥ ነውጥ በኋላ መሆኑ ታውቋል፡፡
የመሬት ነውጡ በርዕደ መሬት መለኪያ ሬክተር ስኬል 8 ነጥብ 8 ሆኖ የተመዘገበ ነበር፡፡
የመስኩ ሊቃውንት በርዕደ መሬቱ እና በእሳተ ገሞራው ክስተቶች መካከል አንዳች ቁርኝት ሊኖር እንደሚችል መገመታቸውን መረጃው አስታውሷል፡፡
የኔነህ ከበደ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s












Comments