top of page

ጥቅምት 1፣2016 - የባህር ማዶ ወሬዎች

  • Oct 12, 2023
  • 2 min read


የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታንያሁ ከተቃዋሚው ብሔራዊ የአንድነት ፓርቲ መሪ ቤኒ ጋንቴዝ ጋር የጦር ወቅት ጊዜያዊ መንግስት ለመመስረት ተስማሙ፡፡


የአገሪቱ ጦር መሰረቱን በጋዛ ሰርፅ ካደረገው የፍልስጤማውያ የጦር ድርጅት ሐማስ ጋር ውጊያ ከገጠመ ዛሬ 6ኛ ቀኑን አስቆጥሯል፡፡


ሐማስ ባለፈው ቅዳሜ ወደ እስራኤል ይዞታዎች በመዝለቅ ድንገት ደራሽ ጥቃት በማድረሱ በእስራኤላውያን ዘንድ ቁጣ እና ድንጋጤ ፈጥሯል፡፡


ኔታንያሁ እና ጋንቴዝ ጊዜያዊውን የጦር ወቅት ካቢኔ ለማቋቋም የተስማሙት የፖለቲካ ተቃርኗቸውን ወደ ጎን በማለት በጋራ ለመቆም እንደሆነ ቢቢሲ ፅፏል፡፡


የዋነኛው ተቃዋሚ የፖለቲካ ማህበር መሪ ያኢር ላፒድ ግን አዲሱን ጥምረት እንዳልተቀላቀሉ ተሰምቷል፡፡


አዲሱ ካቢኔ ጦርነቱ ዳር እስኪደርስ እንደሚዘልቅ በዘገባው ተጠቅሷል፡፡


ኔታንያሁ የሐማስ አባላትን ለወሬ ነጋሪ ሳናስቀር በሙሉ እንጨርሳቸዋለን ማለታቸውንም ቢቢሲ ፅፏል፡፡


የተቃዋሚው መሪ ቤኒ ጋንቴዝም ተመሳሳይ ይዘት ያለው ንግግር ማድረጋቸው ተሰምቷል፡፡


ጋንቴዝም ሐማስን ከእንግዲህ ከምድረ ገፅ እናጠፋዋለን ብለዋል፡፡


አዲሱ ካቢኔ የጦር አመራር ውሳኔዎችን ለማቀላጠፍ እንደሚረዳ ታምኖበታል፡፡


የፍልስጤማውያኑ የጦር ድርጅት ሐማስ በእስራኤል ላይ መጠነ ሰፊ ድንገት ደራሽ ጥቃት ማድረሱ እስራኤልን ክፉኛ ማስቆጣቱ ይነገራል፡፡


የአሜሪካው ፕሬዘዳንት ጆ ባይደን እስራኤል ራሷን የመከላከል መብቷ የተጠበቀ ቢሆንም እርምጃዋ በአለም አቀፍ የጦርነት ህግ ሊመራ ይገባዋል ማለታቸው በዘገባው ተጠቅሷል፡፡



የተባበሩት መንግስታት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ወደ ፍልስጤማውያኑ ጋዛ ሰርፅ እንደ ምግብ ፣ ውሃ እና ነዳጅ ያሉ ለእለት ከእለት ሕይወት አስፈላጊ ነገሮች ሊገቡ ይገባል አሉ፡፡


ጉቴሬዝ ለሰብአዊ አቅርቦትም መንገዶች እንዲከፈቱ መጠየቃቸውን አረብ ኒውስ ፅፏል፡፡


እስራኤል ምግብ ፣ ውሃ እና ነዳጅ ወደ ጋዛ ሰርፅ እንዳያልፍ መከልከሏን ዘገባው አስታውሷል፡፡


ወደ ጋዛ የሚያልፈውንም ኤሌክትሪክ አቋርጣለች፡፡


የእስራኤል እርምጃ ለወትሮውም ሰብአዊ ቀውስ ተለይቶት በማያውቀው ጋዛ ሰርፅ ችግሩን ይበልጥ እንደሚያባብሰው ተሰግቷል፡፡


በዚህም የተነሳ የተባበሩት መንግስታት ዋና ፀሀፊ አንቶኒዮ ጉቴሬዝ ሰብአዊ አቅርቦቱ ግዴታ ሊፈቀድ ይገባል ማለታቸው ተሰምቷል፡፡



የኒጀር ወታደራዊ መንግስት በአገሪቱ የተባበሩት መንግስታት የዲፕሎማሲያዊ ተልዕኮ መሪ ለቀው እንዲወጡ ጠየቁ፡፡


የልዑክ ቡድን መሪው ኒጀርን ለቅቀው እንዲወጡ ከትናንት አንስቶ የ72 ሰዓታት ጊዜ እንደተሰጣቸው አፍሪካ ኒውስ ፅፏል፡፡


የመንግስታቱ ድርጅት የዲፕሎማሲያዊ ተልዕኮ መሪ ኒጀርን ለቅቀው እንዲወጡ የታዘዙት በቅርቡ በተካሄደው 78ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ በተገቢው ሁኔታ እንዳንካፈል መሰናክል ፈጥረዋል ተብለው ነው፡፡


የኒጀር የጦር አለቆች ከ2 ወራት በፊት ቀድሞውን ፕሬዘዳንት ሞሐመድ ባዙምን መንግስት በመገልበጥ ስልጣን መያዛቸው ይታወቃል፡፡


በጠቅላላ ጉባኤው ላይ ተሳትፏቸው የተስተጓጎለው በዚሁ ምክንያት ነው ተብሏል፡፡



የኔነህ ከበደ


የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ… https://bit.ly/33KMCqz

Recent Posts

See All
የሐምሌ 23 2018 የውጪ ሀገር ወሬዎች

#ግብፅ በግብፅ የሜዴትራኒያን የባህር ዳርቻ የነበረ የአሜሪካ የጋዝ ማጠራቀሚያ መርከብ በድሮን ተመታ ተባለ፡፡ ሁለት የደህንነት ምንጮች መርከቡ በድሮን እንደተመታ አረጋግጠውልኛል ሲል ሬውተርስ ፅፏል፡፡ መርከቡ በድሮን እንደተመታ በእሳት መያያዙ ታውቋል፡፡ ቃጠሎው ወደ ሌላ መርከብም ተጋብቶ ነበር ተብሏል፡፡ ኋላ ግን

 
 
 
የሐምሌ 22 2018 የውጪ ሀገር ወሬዎች

#አሜሪካ አሜሪካ እና ሳውዲ አረቢያ ኢራቅ ውስጥ በአፍቃሪ ኢራን ታጣቂዎች ይዞታ ላይ ድብደባ ፈፀሙ፡፡ ሰሞኑን ሳውዲ አረቢያ በኢራቅ የሚገኙ አፍቃሪ ኢራን ታጣቂዎች በድሮን ጥቃት አድርሰውብኛል ስትል እንደነበር አልጀዚራ አስታውሷል፡፡ ሳውዲ ጥቃቱን ከማውገዝ በተጨማሪ መበቀሌ አይቀርም በሚል ዝታ ነበር፡፡ በኢራቆቹ አ

 
 
 
የሐምሌ 21 2018 የውጪ ሀገር ወሬዎች

#ጃፓን የጃፓን ደቡባዊ ምዕራብ ክፍል በርዕደ መሬት ተመታ፡፡ ርዕደ መሬቱ የደረሰው ኩማማቶ የተባለው የአገሪቱ ክፍል እንደሆነ ኒኪ እስያ ፅፏል፡፡ የመሬት ነውጡ የተቀሰቀሰው ከምድር በ10 ኪሎ ሜትር ጥልቀት መሆኑ ታውቋል፡፡ ነውጡ በርዕደ መሬት መለኪያ /ሬክተር ስኬል/ 7 ነጥብ 1 ሆኖ መመዝገቡ ታውቋል፡፡ ቀደም ሲ

 
 
 

Comments


Sheger App Logo
iOS Store
Google Play
  • Facebook
  • X
  • Youtube
  • TikTok
  • Telegram
  • Whatsapp

    ሸገር
102.1

ሸገር ኤፍ ኤም 102.1 አዲስ የሬዲዮ አቀራረብ መላና አዲስ ቃና ይዞ የቀረበ በሀገሪቱ የሚዲያ ገበያ ላይ መሪ ሚና የሚጫወት ጣቢያ ነው፡፡

ሁሌም ከሸገር ጋር ሁኑ
ሸገር የእናንተ ነው
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር! 

Sheger Radio | Sheger 102.1FM  © 2026 Adey Tensae Media & Entertainment PLC.  

bottom of page