ግብርና ለኢትዮጵያ ጥቅል ሀገራዊ ምርት(GDP) ከፍ ያለ ድርሻ የሚያበረከት ሲሆን ለብዙዎችም የስራ ዕድል የፈጠረ ዘርፍ ነው።
- sheger1021fm
- 1 hour ago
- 2 min read
ታህሳስ 9/2018
ግብርና ለኢትዮጵያ ጥቅል ሀገራዊ ምርት(GDP) ከፍ ያለ ድርሻ የሚያበረከት ሲሆን ለብዙዎችም የስራ ዕድል የፈጠረ ዘርፍ ነው።
ለዚህ ዘርፍ እየቀረበ ያለው ብድር ግን ከአስር በመቶ በታች መሆኑ ተነግሯል።
ግብርና ከኢትዮጵያ ጥቅል ሀገራዊ ምርት ከ32 በመቶ በላይ የሚሆነውን ድርሻ እንደሚሸፍን መረጃዎች ያሳያሉ።
ከወጪ ንግድ ከሚገኘው ገቢም ከ80 በመቶ የሚልቀው ከዚሁ ዘርፍ የሚገኝ እንደሆነ ተነግሯል።
ዘርፉ ከኢትዮጵያ ህዝብ ከ62 በመቶ ለሚልቀው የስራ ዕድል መፍጠሩም ይጠቀሳል።
በአጠቃላይ ኢኮኖሚ ውስጥ እንዲህ አይነት ጉልህ ድርሻ ላለው ለዚህ ዘርፍ እየቀረበ ያለው ብድር ግን ዝቅተኛ እንደሆነ፤ የኢትዮጵያ አበባ ፤ አትክልትና ፍራፍሬ አምራቾች እና ላኪዎች ማህበር ዋና ዳይሬክተር አቶ ቴዎድሮስ ዘውዴ ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ ካለው አጠቃላይ የፋይናንስ አቅርቦት ለግብርና የዋለው ከ10 በመቶ በታች ነው ብለዋል።

የገንዘብ ተቋማት ለግብርናው ዘርፍ በበቂ መጠን ብድር የማያቀርቡበት አንዱ ምክንያት የመመለስ ስጋት አለበት የሚል እንደሆነ አቶ ቴዎድሮስ ተናግረዋል።
ዘርፉ በቂ የፋይናንስ ድጋፍ ቢያገኝ ውጤታማ ሊሆን እንደሚችል የአበባ እርሻዎች ማሳያ ናቸው የሚሉት አቶ ቴዎድሮስ፤ ከልማት ባንክ ባገኙት ብድር ኢትዮጵያን ከአለም አምስት ትላልቅ አበባ አምራች ሀገራት ተርታ እንዳሰለፏት ተናግረዋል።
አበባ አምራች ባለሃብቶች አሁን ላይ ብዙ የብድር አቅርቦት ችግር የለባቸውም የሚሉት አቶ ቴዎድሮስ እየተፈተኑ ያሉት የአትክልትና ፍራፍሬ እርሻዎች እንደሆኑ ተናግረዋል።
ለግብርናው ዘርፍ በቂ ብድር እንዲቀርብ ከመንግስት እና ከባንኮች ጋር በተለያዩ ጊዜያት ውይይቶች መደረጋቸውን የተናገሩት ዳይሬክተሩ አንዳንድ በጎ ጅምሮችም አሉ ብለዋል።
ፍላጎታችን ግን በተፋጠነ ሁኔታ ነገሮች እንዲሻሻሉ ነው ሲሉ አክለዋል።
በኢትዮጵያ የግብርናው ዘርፍ በያመቱ 2 ነጥብ 5 ትሪሊየን ብር ብድር ይፈልጋል ተብሏል።
ባለፈው የጎርጎርሳውያኑ 2024 ግን ባንኮች እና የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት ለዘርፉ የሰጡት ብድር ግን 52 ቢሊየን ብር እንደሆነ ተነግሯል።
መንግስት በበኩሉ ከአምስት ዓመት በኋላ ለዘርፉ የሚሰጠው ብድር ቢያንስ 881 ቢሊየን ብር እንዲደርስ ግብ አስቀምጧል።
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ…..
ንጋቱ ረጋሣ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
Telegram : https://t.me/ShegerFMRadio102_1
Facebook፡ https://web.facebook.com/Sheger102.1








