top of page

የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት 30.65 ቢሊዮን ዶላር የሚጠይቅ የኃይል ማስፋፊያ ዕቅድ ይፋ አደረገ።

  • 30 minutes ago
  • 1 min read

ሐምሌ 20 2018


የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት 30.65 ቢሊዮን ዶላር የሚጠይቅ የኃይል ማስፋፊያ ዕቅድ ይፋ አደረገ።


እቅዱ የኔትወርክ ማሻሻያ እና ማስፋፊያ፣ የሰብስቴሽን እና ተያያዥ የመሰረተ ልማት ግንባታዎች፣ ስማርት ግሪድ እና ቆጣሪ ማስፋፋትን እንደሚያካትት አገልግሎቱ ዛሬ ይፋ አድርጓል፡፡


የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የመጭውን የ25 አመት የሀይል ፍላጎት ለማወቅ የሚያግዝ ጥናት ማስጠናቱን ጠቅሷል፡፡


በፍጥነት እያደገ የመጣውን የሀይል ፍላጎት ለመሸከም፣ የኔትዎርክ ችግርን ለመፍታትና የሥርጭት ሥርዓትን ወደ ዘመናዊ እና ዲጅታል አሰራር ለማሸጋገር የ25 አመታት ሀገር አቀፍ የስርጭት ስርዓት ማሻሻያና ማስፋፊያ ማስተር ፕላን ጥናት መጠናቱ ተጠቅሷል፡፡


ጥናቱም በአለም ባንክ የገንዘብ ድጋፍ እና ሞኔንኮ ኢራን ኢንጅነሪንግ ኮንሰልቲንግ በተሰኘ የኢራን አማካሪ ድርጅት መጠናቱን ሲነገር ሰምተናል።


ማስተር ፕላኑ የመጪዎቹን 25 አመታት የሚሸፍን መሆኑ የተነገረ ሲሆን የአጭር፣ የመካከለኛና የረጅም ጊዜ የኔትወርክ ማሻሻያ፣ ማስፋፊያ፣ ዲጂታል ሽግግርና ኢንቨስትመንት ፍላጎቶችን ለይቷል ተብሏል።


ጥናቱም 1 ሺህ 100 መጋቢ መስመሮች፣ 183 ሰብስቴሽኖች እና 79 ሺህ ኪ.ሜ ነባር መካከለኛ መስመር ዳሰሳ ማደረጉን ያነሳው የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ አገልግሎት የህዝብ ቁጥር እድገትን፣ የነፍስ ወከፍ የኢነርጂ ፍላጎትን ጨምሮ የቴክኖሎጂ እድገት የሚጠይቀውን የኤሌክትሪክ ሀይል ፍላጎት ከግምት ውስጥ ያስገባ ነው ብሎታል።


ጥናቱ ውስጥ ከተካተቱት 1 ሺህ 100 መጋቢ መስመሮች 271 ያህሉ የቮልቴጅ መጠናቸው ያልተመጣጠነ መሆኑን የሚያሳየው የጥናቱ ውጤት፣ ከእነዚህ ውስጥ 182 ያህሉ የሀይል ጭነት የበዛባቸው እንደሆኑ ጠቁሟል።


በማሰራጫ መስመሮች ላይ በተጠናው ጥናት መሰረት ደግሞ 6 ሺህ 800 ትራንስፎርመሮች፣ 15 ሺህ 800 የመካከለኛ መስመር ተሸካሚ ምሰሶዎች፣ 6 ሺህ 833 በአየር ላይ የተዘረጉ መስመሮች እና 638 መካከለኛ መስመር መቆጣጠሪያዎች ላይ ማስተካከያ ግኝት የተገኘባቸው እንደሆነ ተናግሯል።


እነዚህም እና ሌሎች የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማቶች ላይ የሚታዩ ችግሮችን መለየት ኢትዮጵያ በቀጣይ 25 አመታት አስተማማኝ የስርጭት ሥርዓት እና የሀይል አቅርቦት እንዲኖራት ያደርጋል ተብሎ እንደታመነበት አገልግሎቱ ተናግሯል።


ፋሲካ ሙሉ ወርቅ

Comments


Sheger App Logo
iOS Store
Google Play
  • Facebook
  • X
  • Youtube
  • TikTok
  • Telegram
  • Whatsapp

    ሸገር
102.1

ሸገር ኤፍ ኤም 102.1 አዲስ የሬዲዮ አቀራረብ መላና አዲስ ቃና ይዞ የቀረበ በሀገሪቱ የሚዲያ ገበያ ላይ መሪ ሚና የሚጫወት ጣቢያ ነው፡፡

ሁሌም ከሸገር ጋር ሁኑ
ሸገር የእናንተ ነው
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር! 

Sheger Radio | Sheger 102.1FM  © 2026 Adey Tensae Media & Entertainment PLC.  

bottom of page