የከተሞች መስፋፋትን ተከትሎ የመሬት አጠቃቀም ላይ የሚታዩ ክፍተቶች የአርሶአደሮች የመሬት ይዞታ መብት መጠበቅ ላይ መሰራት አለበት ተባለ።
- sheger1021fm
- 4 hours ago
- 1 min read
ታህሳስ 16/2018
በኢትዮጵያ የከተሞች መስፋፋትን ተከትሎ የመሬት አጠቃቀም ላይ የሚታዩ ክፍተቶች በተለይም የአርሶአደሮች የመሬት ይዞታ መብት መጠበቅ ላይ መሰራት አለበት ተባለ።
ከመሬት አስተዳደር ጋር በተገናኘ ዘመናዊ አሰራሮችን በመከተል አርሶአደሩን በመሬቱ ተጠቃሚ እንዲሆን ማድረግ ያስፈልጋል ተብሏል።
ይህ የተባለው 3ተኛውን የኢትዮጵያ የመሬት ቀን አስመልክቶ ላንድ ፎር ላይፍ በተባለ ሀገር በቀል ተቋም በተሰናዳ የፓናል ውይይት ላይ ነው።
ላንድ ፎር ላይፍ ኢትዮጵያ፣ በመሬት አስተዳደር እና ኃላፊነት የተሞላበት የግብርና ኢንቨስትመንቶች ላይ የሚሰራ ድርጅት ነው ተብሏል።

ምክክሩ የኢትዮጵያ የመሬት አስተዳደር ተቋማዊ እና የሕግ ማዕቀፎች ወቅታዊ ሁኔታዎች ፣ በፖሊሲ ጉዳዮች፣ የከተማ መሬት አስተዳደር ፣ ኃላፊነት በተሞላበት የግብርና ኢንቨስትመንት ላይ እየተካሄደ ነው።
በኢትዮጵያ አርሶአደሩ ከመሬቱ ተጠቃሚ እንዲሆን በዘመናዊ መንገድ የገጠር መሬት አስተዳደር እና አጠቃቀም በተመለከተ በግብርና ሚኒስቴር በኩል ለአርሶ አደሩ ማረጋገጫ በመስጠትና በመመዝገብ ተጠቃሚ እንዲሆን እየተደረገ ነው ተብሏል።
ከተሞች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ መስፋፋታቸው በተለይም ለነሱ ቅርብ የሆኑ የእርሻ መሬቶች መጋፋታቸው የአርሶ አደሩን የመሬት መብት ተጠቃሚነት የሚጎዳ በመሆኑ የመሬት አስተዳደር ስርአቱ ይህንን ታሳቢ በማድረግ መስራት እንደሚጠበቅበት ተነግሯል።
ከአርብቶ አደሩ የመሬት ባለቤትነት ጋርም በተመሳሳይ የህዝብ ቁጥርና የእንስሳት ብዛት መጨመር ተከትሎ የመሬት አጠቃቀም ስርዓቱ እየተለወጠ መምጣቱን በመድረኩ ላይ በቀረበ ጥናት ተጠቅሷል።
በየክልሉ ያለው የመሬት ሀብት በአግባቡ ተመዝግቦ መሬት የግጭት መነሻ እንዳይሆንና እንዳይባክን አርሶአደሩ ከመሬቱ እንዲጠቀም በግብርና ሚኒስቴር በኩል የተጀመሩ ስራዎች ሊቀጥሉ ይገባል ተብሏል።
የኢትዮጵያ የመሬት ቀን አስመልክቶ በተሰናዳው የፓናል ውይይት ላይ አርሶአደሮች ፣ የክልል የግብርና ቢሮ ሃላፊዎች ፣ የመሬት አስተዳደር ባለሙያዎች እና መምህራን ተገኝተዋል።
ምህረት ስዩም
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
Telegram : https://t.me/ShegerFMRadio102_1
Facebook፡ https://web.facebook.com/Sheger102.1








