የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በባንኩ ከሚፈፀመው የገንዘብ ልውውጥ ውስጥ 90 በመቶው የሚላወሰው በዲጂታል መንገድ ነው አለ።
- sheger1021fm
- 3 hours ago
- 1 min read
ህዳር 11 2018
የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በአሁኑ ጊዜ በባንኩ ከሚፈፀመው የገንዘብ ልውውጥ ወይም ግብይት ውስጥ 90 በመቶ የሚሆነው የሚላወሰው በዲጂታል መንገድ ነው አለ።
ይህም ከቀዳማዊ ዓመት ጋር ሲነፃፀር የ17 በመቶ ብልጫ አለው ተብሏል።
የባንኩ አብዛኛው ግብይት በዲጂታል መንገድ በመሆኑ ለሳይበር ጥቃት ተጋላጭነቱ በዚያው ልክ ከፍ እያለ መምጣቱ ይታወቃል ሲሉ የባንኩ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ኤፍሬም መኩሪያ ሲናገሩ ሰምተናል።
አቶ ኤፍሬም ይህንን ያሉት ባንኩ የሳይበር ደህንነት ወርን በማስመልከት ባዘጋጀው ፕሮግራም ላይ ነው።

በ2017 በጀት ዓመት በኢትዮጵያ የፋይናንስ ተቋማት በዲጂታል መንገድ ከተገላበጠው 17.7 ትሪሊዮን ብር ውስጥ 13 ትሪሊዮን ብር ወይም 73 በመቶ ድርሻ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሆኑንም አቶ ኤፍሬም አስረድተዋል።
የባንኩ ግብይት በአብዛኛው ዲጂታል እየሆነ ከመምጣቱ ጋር ተያይዞ ከሚገጥሙ ስጋቶች መካከል የሳይበር ጥቃትና የዲጂታል ማጭበርበር መሆናቸውን ምክትል ፕሬዚዳንቱ ጠቅሰዋል።
የሚሰነዘሩ የሳይበር ጥቃቶችን ለመመከት ባንኩ ለደህንነት እና ስጋት ቅድሚያ ሰጥቶ እየሰራ መሆኑም ተነግሯል።
ሰው ሰራሽ አስተውህሎት (AI) በመጠቀም የሳይበር ስጋቶችን አስቀድሞ ለመለየት፣ለመከላከል እና ምላሽ ለመስጠት የኢትዮጵያ ንግድ ባንኩ እየሰራ መሆኑን አቶ ኤፍሬም አስረድተዋል።
አንድ የሳይበር ጥቃት ለመሰንዘር 39 ሴኮንድ ብቻ እንደሚፈጅ፣ እየተጠናቀቀ በሚገኘው የፈንጆቹ 2025 ዓመት አለም በሳይበር ጥቃቶች ከ10 ትሪሊዮን ዶላር በላይ እንደምታጣ በመድረኩ ሲነገር ሰምተናል።
ንጋቱ ሙሉ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
👇👇👇
🌐Website፡ https://www.shegerfm.com/
🎥YouTube https://tinyurl.com/37tux478
🟦Telegram https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📘Facebook፡ https://tinyurl.com/4tx8t8wm
💬WhatsApp ፡ https://tinyurl.com/ycxjmm3s












Comments