የተከለከለው ትልቅ ትንሽ፤ ወፍራም ስስ ተብሎ ሳይሆን ሁሉም አይነት የፕላስቲክ ከረጢት መሆኑን የአዲስ አበባ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ተናገረ፡፡
- 11 minutes ago
- 2 min read
የካቲት 10/2018
የተከለከለው ትልቅ ትንሽ፤ ወፍራም ስስ ተብሎ ሳይሆን ሁሉም አይነት የፕላስቲክ ከረጢት መሆኑን የአዲስ አበባ አካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ተናገረ፡፡
ባለስልጣኑ ሁሉንም አይነት የከረጢት ፕላስቲክ ይዞ የተገኘ በአዋጅ 1383/2017 መሰረት ከ2000 ብር በማያንስ እና ከ5000 ብር የማይበልጥ ገንዘብ እንደሚቀጣ አሰረድቷል፡፡
የአካባቢ ጥበቃ በለስልጣን "ህግን እናውቃለን" በማለት የተከለከለው ስስ ፌስታል ብቻ ነው ከሚሉ አሳሳች አካላት ህብረተሰቡ እራሱን እንዲጠብቅ አሳስቧል፡፡
ባለስልጣኑ ይህን ያሳሰበው ዛሬ የፕላስቲክ ከረጢትን የሚተካ ከፕላስቲክ ውጭ ከረጢቶችን ከሚያመርቱ አካላት ጋር ባካሄደው ውይይት ላይ ነው፡፡
በውይይቱ ላይ ፕላስቲክ በአገር ኢኮኖሚ፣ጤና እና ማህበራዊ ጉዳይ ላይ እያደረሰ ያለውን ቀውስ አስመልክተው የውይይት መነሻ ጸሁፍ ያቀረቡት የባለስልጣኑ የህግ ተከባሪነት ዳይሬክተር አቶ ለሜሳ ጉደታ በአለም ደረጃ በፕላስቲክም ሆነ በሎሎች ምክንያቶች በሚፈጠር ብክለት ወደ 9 ሚሊዮን ሰዎች ይሞታሉ ብለዋል፡፡

በአዲስ አበባ ብቻ ከሚመነጨው ደረቅ ቆሻሻ ውሳጥ 13 በመቶ የሚሆነው ከፕላስቲክ ቁሶች ነው ሲሉ አቶ ለሜሳ ተናግረዋል፡፡
በዓመት 80ሺህ ቶን ፕላስቲክ ይመረታል ተብሎ ይገመታል የሚሉት የባለስልጣኑ የህግ ተከባሪነት ዳይሬክተር አቶ ለሜሳ ጉደታ ከዛ ውስጥ በዑደት ተመልሶ ለአገልግሎት የሚበቃው 5 በመቶው ብቻ ነው ይላሉ፡፡
ቀሪው ለዳግም አገልግሎት አይውልም ብለዋል፡፡
የፕላስቲክ ከረጢት ተመልሶ ለአገልግሎት አይውልም ወይንም ሪሳይክል አይሆንም ይህን ተግባር የሚያከናውኑትም አይፈልጉትም ለዚያ ነው የፕላስቲክ ከረጢት የተከለከለው ሲሉ አቶ ለሜሳ አክለዋል፡፡
የፕላስቲክ ከረጢት ሲቃጠል አየርን ይበክላል፣ሲጣልም አይበሰብስም ለመሬት አይሆንም ሳይበሰብስ አፈር ውስጥ 100 ዓመት ይቀመጣል ይህን ችግር ለመፍታት የፕላስቲክ ከረጢትን ማምረትም ሆነ መጠቀምን ሙሉ በሙሉ መከልከል አስፈልገዋል ተብሏል፡፡
ህጉን አላግባብ ከሚተረጉሙት ሰዎች እራሳችሁን ጠብቁ ያለው ባለስልጣኑ ለአንድ ጊዜ ብቻ የሚያገለግል ማለት ስስ ከረጢት ማለት ሳይሆን በሪሳይክል ተመልሶ የማይቀየር ማለት እንደሆነ መታወቅ አለበት ብሏል፡፡
በዚህም መሰረት የትኛውም አይነት ማለትም ስስም ይሁን ወፍራም ትልቅም ይሁን ትንሽ የፕላስቲክ ከረጢትን ያመረተ ከ50ሺህ ብር የማያንስ እና ከ200 ሺህ ብር በማይበልጥ ገንዘብ ይቀጣል፣ይዞ ከተገኘ ደግሞ ከ2000 ብር በማያንስ እና ከ5000 ብር በማይበልጥ ገንዘብ ይቀጣል ብሏል።
ያሬድ እንዳሻው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
X :- https://x.com/shegerfm?s=2
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7








