የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ የፋይናንስ ተቋም ኪሳራ ላይ ሲወድቅ ለገንዘብ አስቀማጮች የሚከፍለውን ኢንሹራንስ ከፍ ለማድረግ እያሰበበት እንደሚገኝ ተናገረ፡፡
- sheger1021fm
- 15 hours ago
- 2 min read
ጥር 29/2018
የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ የፋይናንስ ተቋም ኪሳራ ላይ ሲወድቅ ለገንዘብ አስቀማጮች የሚከፍለውን ኢንሹራንስ ከመቶ ሺህ ብር ከፍ ለማድረግ እያሰበበት እንደሚገኝ ተናገረ፡፡
አሁን ላይ ኪሳራ ለደረሰበት አንድ የማይክሮ ፋይናንስ ተቋም ገንዘብ አስቀማጮች ኢንሹራንስ እየከፈልኩ እገኛለሁም ብሏል፡፡
የኢትዮጵያ የተቀማጭ ገንዘብ መድን ፈንድ በባንኮች እና በማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት ገንዘብ ላስቀመጡ ግለሰቦች እና ድርጅቶች ፤ የኢንሹራንስ ሽፋን በመስጠት ለገንዘብ አስቀማጮች ጥበቃ ለማድረግ የተቋቋመ ነው።
ከተቋቋመ ወደ ሶስት ዓመት እየተጠጋ ሲሆን በዚህ ጊዜ ውስጥ በአጠቃላይ ከአባል ፋይናንስ ተቋማት የሰበሰበው አረቦን 17 ነጥብ 80 ቢሊየን ብር መድረሱን ሠምተናል።

እስከ አሁን ከተሰበሰበው አጠቃላይ አረቦን ውስጥ 16 ነጥብ 20 ቢለየን ምር ከመደበኛ ተቀማጭ ቀሪው 1 ነጥብ 6 ቢሊየን ብር ደግሞ፤
ከወለድ ነጻ ተቀማጭ ገንዘብ የተሰበሰበ እንደሆነ የፈንዱ የኦፕሬሽን ዳይሬክተር አቶ መርጋ ዋቆያ ነግረውናል።
8 ነጥብ 97 ቢሊየን ብር ከግል ባንኮች ፤ 8 ነጥብ 63 ቢሊየን ብር ከኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፤ ቀሪው 0 ነጥብ 21 ቢሊየን ብር ከማክሮፋይናነስ ተቋማት የተሰበሰበ እንደሆነ አክለዋል።
በ2018 በጀት ዓመት የመጀመሪያዎቹ ስድስት ወራት 3 ነጥብ 74 ቢሊየን ብር አረቦን ተሰብስቧልም ብለውናል።
ባንኮችና የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት ለፈንዱ አረቦን የሚከፍሉት በተቀማጭ ገንዘብ ልክ እንደሆነም አቶ መርጋ ነግረውናል።
እስከ አሁን በኪሳራ ምክንያት ፈንዱ ኢንሹራንስ እየከፈለ ያለው ለአንድ ማይክሮ ፋይናንስ አስቀማጮች እንደሆነ አቶ መርጋ ነግረውናል።
አንድ ባንክ ወይም የማክሮ ፋይናንስ ተቋም ቢከስር ፈንዱ ለአስቀማጩ የሚከፍለው እስከ መቶ ሺህ ብር ነው።
ቀሪው የአስቀማጩ ገንዘብ የከሰረው ተቋም ንብረት ተጣርቶ እንዲሸጥ በማድረግ የሚከፈል ነው ተብሏል።
በፈንዱ የሚከፈለው ኢንሹራንስ ከመቶ ሺህ ብር ከፍ እንዲል ጥያቄዎች እየቀረቡ እንደሆነ የተናገሩት አቶ መርጋ እኛም እያሰብንበት ነው ብለውናል።
የፈንዱ ጠቅላላ ኢንቨስትመንት 19.77 ቢሊየን ብር መድረሱንም አቶ መርጋ ነግረውናል።
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ…..
ንጋቱ ረጋሣ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7












Comments