የብር ኖትን በሃገር ውስጥ ማሳተም ካለው ክብደት አንፃር ወይስ ትኩረት ያለ መስጠት ችግር?
- sheger1021fm
- 2 hours ago
- 2 min read
ጥር 13/2018
መንግስት እስከ ዛሬ በውጪ የሚታተመውን የኢትዮጵያ የብር ኖቶች በሃገር ውስጥ የማተም ዕቅድ እንዳለው ተናግሯል።
ይህም የብር ኖቶችን በውጪ ሃገራት ለማሳተም ሀገር የምታወጣውን ወጪ ያስቀርላታል ተብሏል።
ለመሆኑ የብር ኖቶችን በሃገር ውስጥ ማተም በቢሊዮን ዶላሮች የሚያስወጣውን ወጪ የሚቀንስ ከሆነ እስከ ዛሬስ በውጪ ሃገር ማሳተሙ ለምን ተመራጭ ሆኖ ቆየ?
የብር ኖትን በሃገር ውስጥ ማሳተም ካለው ክብደት አንፃር ወይስ ትኩረት ያለ መስጠት ችግር?
የምጣኔ ሃብት ባለሙያው አቶ ጥላሁን ግርማ ለዘርፉ ትኩረት ያለመስጠት ችግር ነው የሚል ምላሽ አላቸው።
ባለሙያው መንግስታት የራሳቸው ቅድሚያ የሚሰጡአቸው ጉዳዮች ስሏሏቸው እስከ ዛሬም የብር ኖቶችን በሃገር ውስጥ ማሳተም ብዙም ትኩረት ሳይሰጡት ቆይተው ሊሆን ይችላል? የሚል ሙያዊ ግምታቸውን ያስቀምጣሉ።
የምጣኔ ሃብት ባለሙያው አቶ ጥላሁን፤ በእርግጥ የብር ኖቶችን በሀገር ውስጥ ማምረት እንደ ጥቅሙ ሁሉ ጉዳቱና ፈተናውም የበዛ ነው ይላሉ።

ባለሙያው የብር ኖቶችን የጥራት ጉዳይ እንደ አንድ ፈተና ያነሳሉ።
ብዙ ገንዘብ ከፍለን በውጪ ሃገር የምናሳትማቸው የብር ኖቶቻችን እንኳን በአጭር ጊዜ ውስጥ አርጅተውና ተቀዳደው እየተቸገርን ነው የሚሉት ባለሙያው በሃገር ውስጥ ሲታተም ደግሞ ሀገር ካላት የማተም ልምድና የቴክኖሎጂ ግብዓት አንፃር ጥራቱ ምን ድረስ ሊሆን ይችላል? የሚለው ሊታሰብበት ይገባል ይላሉ።
የብር ኖቶች በየጊዜው እያረጁ የሚጣሉ ከሆነ፤ ዞሮ ዞሮ ይህም በውጪ ሃገር ከማሳተሙ ያልተናነሰ ሌላ ወጪ ሊሆን እንደሚችል አቶ ጥላሁን ያስረዳሉ።
ባለሙያው ሌላው እንደ ፈተና የሚያነሱት የብር ኖቶችን የማሳተሚያ ግብዓት አቅርቦትን ነው።
የብር ኖቶችን ለማተም ከሚረዱ ግብዓቶች አንዱ ጥጥ ነው የሚሉት አቶ ጥላሁን፣ ኢትዮጵያ ጥጥ ላኪ ሃገር እንደመሆኗ በዚህ ላንቸገር እንችላለን፤ ነገር ግን እንደ ማቅለሚያ ያሉ ሌሎች ግብአቶችን ከውጪ ማስመጣታችን አይቀርም ይላሉ።
ይህ ደግሞ ሌላ ወጪ እና የሌላ ሃገር ግብዓት ላይ ጥገኛ ስለሚያደርገን ሊታሰብበት እንደሚገባ ይመክራሉ።
አቶ ጥላሁን ግርማ የብር ኖቶችን በሀገር ውስጥ ማተም ሌለኛው ፈተና የብር ኖቶችን እያተሙ እንደ ፈለጉ በገበያ ውስጥ የመበተን ጎጂ አሰራርን ሊያመጣ ይችላል ይላሉ።
ይህም መመለሻ ለሌለው የዋጋ ግሽበትና ጥቂት ሰዎች ብቻ ኪሳቸውን የሚያሳብጡበትን የኢኮኖሚ ውድቀት ስለሚያመጣ ይህንን የሚቆጣጠር ጠንካራና ተዓማኒ ሀገራዊ ተቋም እንዴት መፍጠር እንችላለን? ሲሉ ይጠይቃሉ።
ከዚህ ባሻገር ግን የብር ኖቶችን በሀገር ውስጥ ማተም ሀገር ከምታወጣው ከፍተኛ ወጪ እንደሚያድናት እና የሀገርን ሉዓላዊነትም ለማስጠበቅ አዋጭ መላ መሆኑን ባለሙያው አስረድተዋል።
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ….
ንጋት መኮንን
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…..
YouTube : https://url-shortener.me/2DTR
Telegram : https://t.me/ShegerFMRadio102_1
Facebook፡ https://url-shortener.me/2DTY
WhatsApp :https://url-shortener.me/2DU0
Website፡ https://www.shegerfm.com/
LinkedIn :https://url-shortener.me/2DU8
Tiktok : https://url-shortener.me/2DUB
Instagram : https://url-shortener.me/2DUD












Comments