የሰላም እጦት ኢትዮጵያን በቆዳው ዘርፍ ማግኘት የሚገባትን ያህል ገቢ እንዳታገኝ አድርጓታል ሲል የኢትዮጵያ ቆዳ ኢንዱስትሪዎች ማህበር ተናገረ።
- 18 minutes ago
- 2 min read
የካቲት 12/2018
የሰላም እጦት ኢትዮጵያን በቆዳው ዘርፍ ማግኘት የሚገባትን ያህል ገቢ እንዳታገኝ አድርጓታል ሲል የኢትዮጵያ ቆዳ ኢንዱስትሪዎች ማህበር ተናገረ።
ማህበሩ ይህን ያለው ለ15 ኛ ጊዜ የሚያካሄደውን የመላው አፍሪካ የቆዳ ንግድ ትርኢት “ሜሴ ፍራንክፈርት” ከተሰኘ አለም አቀፍ የንግድ ትርኢት አዘጋጅ ጋር በጋራ ለማከናወን ትናንት በስካይ ላይት ሆቴል ባደረጉት ስምምነት ወቅት ነው።
በመድረኩ ላይም በፀጥታ ችግር ምክንያት ከፍተኛ ቆዳ የሚገኝባቸው አካባቢዎች ላይ ቆዳዎችን ለመሰብሰብ ባለመቻሉ በርካታ ቆዳዎች በስብሰው እንደቀሩም ተነግሯል።
በዚህ ምክንያት ኢንደስትሪዎች ማምረት የሚገባቸውን ያህል የቆዳ ውጤቶች እንዳያመርቱ ፥ ሀገርም በዘርፉ ማግኘት የሚገባትን ያህል እንዳታገኝ አድርጎታል ተብሏል።
በዘርፉ የተሰማሩ ኢንደስትሪዎች እየተቸገሩ ያሉበት ሌላኛው ደግሞ የፋይናንስ አቅርቦት እንደሆነም ተነግሯል።
ይህን የነገሩን የኢትዮጵያ የቆዳ ኢንዱስትሪዎች ማህበር ፕሬዚዳንት አቶ ዘላለም መራዊ ናቸው።
ማህበሩ በቆዳው ዘርፍ የሚፈልገውን ያህል ውጤት እንዳይመጣ እንቅፋት ሆነዋል ካላቸው ጉዳዮች መካከል እሴት ሳይጨመር ጥሬ ቆዳ ወደ ውጭ እንዲላክ መፈቀዱ ይገኝበታል።
ይህን በተመለከተም መንግስት እሴት ሳይጨመርበት ጥሬ ቆዳ ወደ ውጭ እንዲላክ መፍቀዱ የቆዳ እጥረት ከመጋጠሙ ባሻገር ኢንዱስትሪዎችን እንደሚያዳክም እና እንደሚጎዳ አቶ ዘላለም ተናግረዋል ።
በኢንዱስትሪ ሚኒስቴር የውጭ ምርቶች ተወዳዳሪነት መሪ ስራ አስፈጻሚ አቶ ዘሪሁን አበበ በበኩላቸው በሰላም እጦት ምክንያት ቆዳዎች እንዳይሰበሰቡና በስብሰው እንዲቀሩ አድርጓል በተባለው ነገር ላይ ከቦታው የደረሰን ሪፖርት የለም ብለዋል። እስካሁንም አሰባሰቡ ላይ የፈጠረው ችግር እንደሌለ ነው የምናውቀውም ይላሉ።
እሴት ሳይጨምርባቸው የሚላኩ ጥሬ ቆዳዎችን በሚመለከት ምላሽ የሰጡት አቶ ዘሪሁን ወደ ውጭ የሚላኩትን መከልከል አንችልም ብለዋል ።
በዚህ ዘርፍ የተሰማሩ ላኪዎች ላይ ጫና ለመፍጠር ግን በጥሬ ቆዳው ላይ ከፍተኛ ቀረጥ እየጨመርንባቸው ቢሆንም መቆም ግን አልቻለም ብለዋል።
የኢትዮጵያ ቆዳ ኢንዱስትሪዎች ማህበር በቅርቡ ለ15 ኛ ጊዜ የሚያካሂደው የመላው አፍሪካ የቆዳ ንግድ ትርኢት በቆዳው ዘርፍ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት፣ በዘርፉ ለተሰማሩ ኢንደስትሪዎችም የገበያ ትስስር ለመፍጠር፣ ሀገርም በዘርፉ ተጠቃሚ የሚያደርጋትን አቅም ለማሳደግ ያለመ እንደሆም ተነግሯል።
የቆዳ ኢንዱስትሪው በአሁኑ ወቅት በዓመት ከ30 እስከ 40 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እያስገኘ እንደሆነም ሰምተናል።
ሙሉ ዘገባውን ያንብቡ….
ፍቅሩ አምባቸው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
X :- https://x.com/shegerfm?s=2
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7











Comments