ባለፉት ዘጠኝ ወራት ለህዳሴ ግድብ 1.2 ቢሊዮን ብር ተሰብሰቧል ተባለ።
- 1 day ago
- 2 min read
ግንቦት 3/2018
ባለፉት 9 ወራት ለህዳሴ ግድብ 1.2 ቢሊዮን ብር ተሰብሰቧል ተባለ።
ይሀም ለመሰብሰብ ከታቀደው ውስጥ ከ50 በመቶ በታች ወይም 1.2 ቢሊዮን ብር ብቻ ነው ተብሏል፡፡
ባለፉት 9 ወራት ሀገሪቱ ከኤሌክትሪክ ሀይል ሽያጭ ወደ 366 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷ ታውቋል፡፡
ይህ የተነገረው የውሃ እና ኢነርጂ ሚኒስቴር ባለፉት 9 ወራት የሰራቸውን ስራዎች ለህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት ባለፈው ሚያዝያ 29/2018 ዓ.ም ባቀረበበት ወቅት ነው፡፡
ጷጉሜ 4/2017 ዓ.ም የግንባታ ስራው ተጠናቅቆ ለተመረቀው ታላቁ ህዳሴ ግድብ 9 ወራት ውስጥ በህዝብ ተሳትፎ፣ በሀገር ውስጥና በውጭ ሀገራት ተሳትፎ በዘጠኝ ወራት ውስጥ 2.58 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ ታቅዶ እንደነበር ለምክር ቤቱ የቀረበው ሰነድ ያሳያል፡፡
ይሁንና የእቅዱን 50 በመቶ ገደማ ወይም 1.24 ቢሊዮን ብር ገቢ መሰብሰብ እንደተቻለ የውሃ እና እነርጂ ሚኒስቴር ባለፈው ለግል ሚዲያዎች ዝግ በነበረው የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ላይ ያቀረበው የ9 ወር እቅድ አፈጻጸም ሪፖርት ሰነድ ይጠቁማል ፡፡
በዚህም መሰረት ከሀገር ውስጥ ቦንድና ስጦታ ከ935 ሚሊዮን ብር በላይ፣ ከዲያሥፖራ ቦንድና ስጦታ ከ167 ሚሊዮን ብር በላይ፣ በ8100 አጭር የሞባይል መልዕክት አገልግሎት ከ58.9 እና ከኢትዮጵያ የኤሌክትሪክ ኃይል የስጦታ አካውንት ከ78.4 ሚሊዮን ብር በላይ መሰብሰብ መቻሉ ተንግሯል፡፡
ይህም ለመሰብሰብ ከታቀደው 2.58 ቢሊዮን ብር ከግማሽ በታች ወይም 1.24 ቢሊዮን ብር ብቻ ነው፡፡
በሌላ በኩል መስሪያ ቤቱ ከኤሌክትሪክ ኃይል ሽያጭ የሚገኝን ገቢ ለማሳደግ እና የውጪ ምንዛሪ ችግርን ለመቅረፍ የሚያስችሉ በርካታ ስራዎች መሰራታቸውን ዘርዝሯል፡፡ ከዚህ ውስጥ የኤሌክትሪክ ሀይል ሽያጭ ገቢ ማሳደግ ይገኝበታል፡፡
በዚህ መሰረትም ከኤሌክትሪክ ሀይል ሽያጭ በዘጠኝ ወራት 314.1 ሚሊዮን ዶላር ለማግኘት ታቅዶ ከእቅዱ በላይ ማለትም 365.99 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እንደተገኘ ሪፖርቱ ያስረዳል፡፡
የተሸጠ የኤሌክትሪክ ኢነርጂ መጠን ለማሳደግ በተሰራው ስራም በዘጠኝ ወራት ውስጥ 23,575 ጊጋ ዋት ሰዓት ለመሸጥ ታቅዶ 24,940 ጊጋ ዋት ሰዓት ተሽጧል፡፡
ይህም ከዕቅድ በላይ ማስካት ተችሏል ተብሏል፡፡
ኢትዮጵያ ለሱዳን፣ ኬንያ እና ጅቡቲ የኤሌክትሪክ ሃይል በሽያጭ እንደምታቀርብ ይታወቃል፡፡
ሀገሪቱ ወደ ታንዚኒያ ለመላክ ከዚህ በፊት ስምምት ማድረጉን እና ሀይል ለመላክ እየተሰራ ያለው ስራም በሂደት ላይ መሆኑ ከዚህ ቀደም ተዘግቧል፡፡
ሶማሊያ እና ደቡብ ሱዳን ደግሞ ከኢትዮጵያ የኤሌክተርክ ኃይል ለመግዛት ጥያቄ ማቅረባቸው ይታወሳል፡፡
ሀገሪቱ ለሽያጭ ወደ ጎረቤት ሀገራት የምትለከው የኃይል መጠን ከምታመርተው 10 በመቶ ያለበለጠውን መሆኑ ይታወቃል፡፡
የኤሌክትሪክ ሀይል የማመንጨት አቅም ማሻሻልን በተመለከተ ደግሞ በዘጠኝ ወራት ውስጥ 1,669 ሜ.ዋ ኃይል ማመንጨት ተችሏል ተብሏል፡፡
በአጠቃላይ ከተለያዩ የሀይል ምንጮች የመነጨ የኤሌክትሪክ ሀይል ከነበረበት 7.910 ሜ.ዋ ወደ 9.580 ሜ.ዋ ለማሳደግ ታቅዶ በዘጠኝ ወራት 1,669 ሜ.ዋ በማመንጨት ወደ 9,579 ማሳደግ እንደተቻለ በሪፖርቱ ተዘርዝሯል፡፡
በዚህም ከውሃ ሀይል የመነጨ ኤሌክትሪክ ሀይል ከነበረበት 7,451 ሜ.ዋ ወደ 9,051 ሜ.ዋ ለማሳደግ ታቅዶ በዘጠኝ ወራት 1,599 ሜ.ዋ በማመንጨት ወደ 9,050 ሜ.ዋ እንዳደገም ተነግሯል፡፡
በንፋስ ሀይል የመነጨ የኤሌክትሪክ ሀይልን ደግሞ ከነበረበት 434 ሜ.ዋ ወደ 504 ሜ.ዋ ለማሳደግ ታቅዶ በዘጠኝ ወራት 45 ሜ.ዋ በማመንጨት ወደ 479 ሜ.ዋ እንዲያድግ ተደርጓል፡፡
ያሬድ እንዳሻው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
X :- https://x.com/shegerfm?s=2
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7





Comments