ባህላዊና የዘመናዊ የአጥንት ህክምና
- sheger1021fm
- 1 hour ago
- 2 min read
ታህሳስ 11/2018
ባህላዊ ህክምና በተለይ ደግሞ የአጥንት ህክምና አሁንም ብዙዎች ይመርጡታል።
የዘመናዊ የአጥንት ህክምና አዋቂዎች ደግሞ በወጌሾች ላይ ቅሬታ ሲያቀርቡ ይሰማል።
ታዲያ ምን ይሻላል?
80 በመቶ ያህል ኢትዮጵያዊ በተለይም በገጠር ነዋሪ የሆነው ህመም ሲገጥመው ከዘመናዊ ይልቅ ባህላዊውን የህክምና ስርዓት መራጭ እንደሆነ ይነገራል ይህም ለሁሉም ዓይነት ህመሞች ቢሆንም በተለይ ከአጥንት ህክምና ጋር በተገናኘ ግን የከተማ ነዋሪዎችም ከዘመናዊ ይልቅ እንደ ባህላዊ ወጌሻ ያሉ የአጥንት ህክምናዎችን ነው የሚመርጡት።
የባህላዊ ህክምና ስራውን በእውቀትና በጥበብ የሚከውኑ ባለሙያዎች እንዳሉ ሁሉ ግን ከስነ ምግባርም ከውቀት ውጪ በመስራት ጉዳት የሚያገኛቸው ብዙ ሰዎች በመኖራቸው ከዘመናዊው ህክምና ጋር የሚቃረን ሀሳብ እየተፈጠረ መሆኑን የሚናገሩ ባለሙያዎች አሉ።
ኢትዮጵያ የባህላዊ ህክምና ስርዓትን በተመለከተ መቆጣጠሪያ ህግ ገና ያላበጀች በመሆኑ ዘርፉን በስርዓቱ ለመቆጣጠር እንዲሁም ያላግባብ የሚሰሩትን ለመቅጣት ክፍተቶች ይታያሉ።
ለመሆኑ ግን ከሁለቱም በኩል የተሻለውን በመውሰድ መስራት ለምን አልተቻለም በህክምናው ዘርፍ የሚነሱት ችግሮችስ የትኞቹ ናቸው? ስንል ከሁለቱም ወገን ያሉ ባለሙያዎችን ጠይቀናል።
ዶክተር መንግስቱ ገብረዮሐንስ በሀዋሳ ዩንቨርስቲ ጤና ሣይንስ ኮሌጅ የአጥንትና መገጣጠሚያ ሀኪም ናቸው በተለይ የአጥንት ህክምና በሁሉም ጤና ተቋማት ላይ አለመገኘቱ ዝቅተኛ የሆነ ምክንያቱም ኢትዮጵያ ውስጥ ህክምና ከኪስ የሚከፈል መሆኑና የጤና ኢንሹራንስ ያልተዳረሰ በመሆኑ አደጋ ሲደርስበት ወዲያውኑ ጤና ተቋም መጥቶ ከፍሎ መታከም ብዙ ሰው አይችልም ለዚህም በአቅራቢያው የሚያገኘውን የባህል ህክምና እንዲጠቀም አድርጎታል ይላሉ።
በተጨማሪም ማበረሰብ ውስጥ የሚነገር ስለ ዘመናዊ የአጥንት ህክምና ትክክል ያልሆኑ ንግግሮች ሁሉ ሰዎች እንዳይመጡ ከዛ ይልቅ እዛው በአካባቢያቸው ያለውን ነገር እንዲጠቀሙ አርጓቸዋልም ይላሉ።
በኢትዮጵያ የባህል ህክምናው ዘርፍ ከዘመናዊው ቀድሞ ከዘመናት በፊት እየተሰራበት የመጣ ቢሆንም ያስቆጠረውን ያህል ዕድሜ ክብር አልተሰጠውም ከአጥንት ህክምና ጋር በተያያዘ የባህላዊ ወጌሻ ህክምና የሚሰጠውን ያህል ጥቅም አልተከበረም የሚሉት ደግሞ በሀገር አቀፍ የባህል መድኃኒት አዋቂዎች ማሀበር የሲዳማ ክልል ሰብሳቢ የሆኑት የባህል ሐኪም አሊ መሐመድ ናቸው።
የባህላዊ ህክምና ዘርፉ ከዘመናዊ ጋር ተቀራርቦ ቢሰራ ብዙ ጥቅም የሚገኝበት ነው ሌሎች በዘርፉ ትልቅ ጥቅም የሚያገኙ እንደ ቻይና ያሉ ሀገራት ለዚህ ምሳሌ ናቸው አብረን ለመስራትም ፍላጎት አለን ይላሉ የባህላዊ ሀኪሙ።
የዘመናዊውም ይሁን ባህላዊ ህክምና ዘርፉ የራሳቸው ክፍተት አለባቸው ነገር ግን ሁለቱንም አቀራርበው የተሻለውን መርጦ ለመስራት ሀሳብ አለን የሚሉት ደግሞ የኢትዮጵያ አጥንት ቀዶ ህክምና ማህበር ፕሬዝዳንት የሆኑት ዶክተር ኤፍሬም ገብረ ሐና ናቸው።
ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ….
ምህረት ስዩም
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
Telegram : https://t.me/ShegerFMRadio102_1
Facebook፡ https://web.facebook.com/Sheger102.1








