top of page

በፌደራል መንግስትና በህወሓት መካከል የቀጠለው ውጥረት ወደ ዳግም አውዳሚ ጦርነት እንዳያመራ የሰላም ጥረቶች እንዲቀጥሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጠይቀዋል

  • sheger1021fm
  • Nov 4
  • 2 min read

ጥቅምት 25 2018


በፌደራል መንግስት እና በህወሓት  መካከል  የቀጠለው ውጥረት ወደ ዳግም አውዳሚ ጦርነት እንዳያመራ ሁሉም ዓይነት የሰላም ጥረቶች እንዲቀጥሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጠይቀዋል፡፡

 

የሰሜን ዕዝ የተጠቃበትን 5ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ በተሰናዳ ፕሮግራም ላይ ንግግር ያደረጉት የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ህወሓት ከፕሪቶሪያ ስምምነት በኋላ ያደረጋቸው “ትንኮሳዎች፣ እምቢ ባይነቶች፣ ስራዎች እና ሴራዎች” ወደ ጦርነት ለመግባት ከበቂ በላይ መሆነቸውን ተናግረው እኛ ምንም ብንታገስ ከተጠቃን ግን መከላከላችን አይቀርም ሲሉ ማለታቸው ይታወሳል፡፡

 

ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ እኛ ብቻ ጦርነትን ማስቀረት አንችልም ሲሉ ተናግረዋል፡፡

 

ree

ይህን አስመልክቶ በጉዳዩ ላይ ሃሳባቸውን የሰጡት የኢትዮጵያ ዜጎች ለማህበራዊ ፍትህ ፓርቲ ኢዜማ ሊቀመንበር ሙሉዓለም ተገኝ (ዶ/ር) ዳግም ጦርነት እንዳይነሳ እንዲሁም የውጭ ሃይል ጣልቃ ገብነትን ለማስቀረት ድርድር እና ሽምግልናን ጨምሮ ሁሉንም ዓይነት የሰላም ጥረቶች እንዲቀጥሉ ጠይቀዋል፡፡

 

የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረንስ(ኦፌኮ) ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ሙላቱ ገመቹ በበኩላቸው የህዝብን ሃብት እና ወጣቱን አላማ ለሌለው ጦርነት ማዋል በምንም መመዘኛ አግባብነት እንደሌለው ሁለቱም አካላት ማወቅ አለባቸው ሲሉ ተናግረዋል፡፡

 

ree

አቶ ሙላቱ ሕወሃትም ሆነ የፌደራል መንግስት ለፈረሙት የሰላም ስምምነት እና ህገ መንግስት መገዛት ፍላጎት ሳይሆን ግዴታ እንደሆነ ማወቅ አለባቸው ሲሉ አክለዋል፡፡

 

በትናንትናው እለት የፕሪቶሪያን የሰላም ስምምነት ሶስተኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ መግለጫ የሰጠው ቅድሚያ ለሰብአዊ መብቶች የተሰኘ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ውጥረቱ በንግግር እንዲፈታ ጠይቋል፡፡

 

ድርጅቱ በማከልም ህዘቡ ጦርነት እንፈልግም፣ ልጆቻችንንም እንሰጥም በማለት ጦርነቱን እንዲከላከል እና እንዲያወግዝ መክሯል፡፡ 

 

ባለፈው ሳምንት ፓርላማ ቀርበው የነበሩት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት በመጣስ እና ህገ መንግስቱን ባለማክበር ህወሓትን መክሰሳቸውን ተከትሎ መግለጫ ያወጣው ሕውሃት የፌደራል መንግስት ጦርነት ለማካሄድ እንቅስቃሴ እያደረገ ነው በሚል መክሰሱ ይታወሳል፡፡

 

ይህን እንቅስቃሴም አለም አቀፉ ማህበረሰብ እንዲያስቆም ጠይቆ ነበር፡፡

 

ከትናንት በስቲያ በጉዳዩ ላይ መግለጫ ያውጣው የአውሮፓ ህብረት ልዑክ በበኩሉ ሁለቱ አካላት በዚህ ዓመት ይደረጋል ተብሎ ከሚጠበቀው ምርጫ አስቀድሞ የስምምነቱ ፈራሚ አካላት ፖለቲካዊ ንግግር እንዲያደርጉ ጠይቋል፡፡

የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…

👇👇👇

 

Comments


Sheger App Logo
iOS Store
Google Play

    ሸገር
102.1

ሸገር ኤፍ ኤም 102.1 አዲስ የሬዲዮ አቀራረብ መላና አዲስ ቃና ይዞ የቀረበ በሀገሪቱ የሚዲያ ገበያ ላይ መሪ ሚና የሚጫወት ጣቢያ ነው፡፡

ሁሌም ከሸገር ጋር ሁኑ
ሸገር የእናንተ ነው
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር! 

Sheger Radio | Sheger 102.1FM  © 2025 Adey Tensae Media & Entertainment PLC.  

bottom of page