በኢትዮጵያ ከሚፈፀመው የትራፊክ ደንብ ጥፋት ብዛት ጋር ሲተያይ የሚቀጣው አሽከርካሪ አነስተኛ ነው ሲሉ የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትሩ ተናገሩ።
- sheger1021fm
- 1 hour ago
- 1 min read
ታህሳስ 7/2018
በኢትዮጵያ ከሚፈፀመው የትራፊክ ደንብ ጥፋት ብዛት ጋር ሲተያይ የሚቀጣው አሽከርካሪ አነስተኛ ነው ሲሉ የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትሩ ተናገሩ።
ሚኒስትሩ ይህን የተናገሩት በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መደበኛ ስብሰባ ላይ ተገኝተው ከአባላቱ ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ዛሬ ታህሳስ 7 ቀን 2018 ዓ.ም ምላሽ በሰጡበት ወቅት ነው።
የምክር ቤት አባሉ አቶ ዳዉድ መሃመድ አሽከርካሪዎች የመንግስት ገቢ እቅድን ለማሳደግ በሚል በትራፊክ እንደሚቀጡ መናገራቸውን አስረድተዋል።

አቶ ዳውድ አሽከርካሪዎች በተለይም በአዲስ አበባ የመንግስት ገቢ ለማሳደግ በሚል እቅድ አሽከርካሪዎች እንቀጣለን የሚል ቅሬታ እንደሚቀርቡ ጠቁመዋል።
ከፍተኛ ገቢ ለማግኝት እንደሚታቀድ፤ እቅዱን ለማሳካት ደግሞ በወሩ አልያም በዓመቱ መጨረሻ ላይ ብዙ አሽከርካሪዎች እንደሚቀጡ ይናገራሉ እውነቱ ይህ የደንብ ማስከበር ሂደት የትራፊክ ስርዓቱን ለማስከበር ነው ወይስ ገቢ እንዲጨምር ነው? ግባቹ የቱ ነው ሲሉ ጠይቀዋል።
ለጥያቄው ምላሽ የሰጡት የትራንስፖርትና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር ሚኒስትር አለሙ ስሜ "በእኛ አገር፣ በእኛ እምነት ቅጣት ነው የሌለው" ሲሉ መልሰዋል።
"ስላልተቀጣ ነው ሰው የሚያጠፋው" ያሉት ሚኒስትሩ ‘’የምናሽከረክር ሰዎች ብንታዘብ ሰው መብራት አያከብርም የሚቆጣጠር ትራፊክ ከሌለ ቀይ መብራትም ይጥሳል" ሲሉ ተናግረዋል።
ቅጣት የሚጣለው ጥፉት ሲፈፀም እንደሆነ ያስረዱት ሚኒስትር አለሙ "ሳያጠፋ ሰው አይቀጣም፤ በዝቷል፣ አንሷል ከማለታችን በፊት አሽከርካሪው ቅጣትን መፍራት አለበት" ብለዋል።
ሰው ካሜራ ተገጥሞ እንኳን አይፈራም ህግንም አያከብርም የተለመደውን ዩኒፎርም የለበሰ ፖሊስ ካላየ በቀር ሲሉ ተናግረዋል።
ሚኒስትሩ አሽከርካሪ ህግን እንዲያከብር ነው መረባረብ ያለብን እንጂ ቅጣት በዛ የሚሊው ከሌሎች ጎረቤት ሀገሮች አንጻር ገና የእኛ አገር ቅጣት በጣም ትንሽ ነው ሲሉ ከምክር ቤት አባል ለተነሳላቸው ጥያቄ መልሰዋል።
‘’ያለአግባብ የሚቀጡ ካለ እነሱን ማረም ይገባል ነገር ግን በእኛ ድምዳሜ ግን ቅጣት ያንሳል" ብለዋል።
ይህ ደግሞ ከጂቡቲ ጋር እንኳን ምን እንደሚመስል ማየት ይቻላል ሲሊ የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስትሩ ተናግረዋል።
ያሬድ እንዳሻው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
Telegram : https://t.me/ShegerFMRadio102_1
Facebook፡ https://web.facebook.com/Sheger102.1








