በአዲስ አበባ ከስራ ቦታ ደህንነትና ጥንቃቄ ጉድለት የተነሳ በዓመት ከ37 እስከ 75 ሰዎች እንደሚሞቱ ጥናት አሳየ።
- sheger1021fm
- 1 hour ago
- 1 min read
ታህሳስ 9/2018
በአዲስ አበባ ከስራ ቦታ ደህንነትና ጥንቃቄ ጉድለት የተነሳ በዓመት ከ37 እስከ 75 ሰዎች እንደሚሞቱ ጥናት አሳየ።
በከተማዋ ካሉ አምራች ኢንዱስትሪዎ ውስጥ 76 በመቶዎቹ ለሞት፣ ለጤና ችግርና የአካል ጉዳት አጋላጭ ናቸው ተብሏል።
ይህ የተባለው አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፤ ከአዲስ አበባ ሥራና ክህሎት ቢሮ ጋር በመሆን በሥራ ቦታ ደህንነትን ላይ አተኩረው ያደረጉትን ጥናት ባቀረቡበት መድረክ ላይ ነው።
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጥናት ቡድኑ ተሳታፊ የሆኑት ካሱ ጂልቻ በአምራች ኢንዱስትሪዎችና የግንባታ ቦታዎች ያለው የድምፅ ብክለት፣ የሙቀት እና የብርሃን መጠን ከተቀመጠለት ገደብ ከሁለት እና ሶስት ዕጥፍ በላይ ነው ብለዋል።

በዚህም ምክንያት በአምራች ኢንዱስትሪዎች ውስጥ ከሚሰሩ ሰራተኞች 41 በመቶዎቹ የመስማት ችግር አንዳጋጠማቸው፣ 34 በመቶዎቹ ደግሞ የመተንፈሻ አካላት የጤና ጉዳት እንዳለባቸው የጥናቱ ሪፖርት አሳይቷል ተብሏል።
እንደ ባንክ እና ቴሌኮም ባሉ የአግልግሎት መስጫ ተቋማት ውስጥ ከሚሰሩ ሰራተኞች ደግሞ፤ ከስራ ቦታ የአቀማመጥ እና እንቅስቃሴ አለመመቻቸት የተነሳ 69 በመቶዎቹ የመገጣጠሚያና የወገብ ህመም እንዳለባቸው ተነግሯል።
60 በመቶዎቹ ደግሞ የጭንቀትና ድባቴ ስነልቦናዊ ችግር አንዳጋጠማቸው ተጠቅሷል።
ጥናቱ በከተማዋ ባሉ ከ500 በላይ የኢንዱስትሪ እና የአግልግሎት ሰጪ ተቋማትና ከ1,500 በላይ ሰራተኞች ላይ ግብዓት ተሰብስቦ የተሰራ መሆኑን ሰምተናል።
ንጋት መኮንን
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
Telegram : https://t.me/ShegerFMRadio102_1
Facebook፡ https://web.facebook.com/Sheger102.1








