በአየር ንብረት ለውጥ፣ ስርዓተ ምግብና ስርዓተ ፆታ ተፅዕኖ ምክንያት የሚፈጠሩ ችግሮች ለመፍታት ሶስቱንም በአንድ ላይ መስራት ይገባል ተብሏል፡፡
- sheger1021fm
- 2 days ago
- 2 min read
ታህሳስ 14/2018
በአየር ንብረት ለውጥ፣ ስርዓተ ምግብና ስርዓተ ፆታ ተፅዕኖ ምክንያት የሚፈጠሩ ችግሮች እርስ በርስ የተሳሰሩ በመሆናቸው ችግሩን ለመፍታት ሶስቱንም በአንድ ላይ መስራት ይገባል ተብሏል፡፡
በአየር ንብረት ለውጥ ችግር ምክንያት የስርዓተ ምግብ መዛባት ይከሰታል፤ በዚህ ምክንያት የሚመጣው የምግብ እጥረትና ሌላውም ችግር ይበልጡን ሴቶችና ህፃናት ላይ እንደሚበረታ ጥናት አሳይቷል፡፡
የማህበራዊ ጥናት መድረክ (ፎረም ፎር ሶሻል ስተዲስ) በቀረበ ጥናት በአንደኛው ምክንያት የሚፈጠረው ችግር ሌላኛውን እያባባሰው ነው፤ ይሁንና ይህንን በአንድ አስተባብሮ የሚሰራ ተቋም በጣም ጥቂት መሆኑ ታይቷል ብሏል፡፡
ተቋሙ ለ1 ዓመት ከ6 ወራት ያህል ጂካን (GCAN) በተባለው ፕሮጀክት በከወነው በዚህ ጥናት ላይ ጉዳዩ ይመለከታቸዋል የተባሉ 15 ተቋማት መሳተፋቸውን የነገሩን በፎረም ፎር ሶሻል ስተዲስ የጂካን ፕሮጀክት አስተባባሪና በጥናቱ ከተሳተፉት መካከል የሆኑት ሰላም ኢሳያስ (ዶ/ር) ናቸው፡፡

በተለይ በመንግስት ተቋማት እነዚህ ሶስቱንም ጉዳዮች በአንድ አስተባብሮ የሚሰራ ባለሙያ እጥረት የተፈጠረው በአብዛኛው ባለሙያዎቹ አንዱ መስክ የሰረጠኑ ስለሚሆኑ፣ ያሉት ባለሙያዎችም ቢሆኑ ለተሻለ ገቢ በሚል በብዛት ተቋሙን ስለሚለቅቁ፤ በአየር ንብረት ለውጥ፣ ስርዓተ ምግብና ስርዓተ ፆታ ተፅዕኖ ምክንያት የሚፈጠሩ ችግሮችን ከመሰረቱ እንዳይፈቱ ማድረጉን ጥናቱ አሳይቷል ያሉን ሌላው በጥናቱ የተሳተፉትና በአለም አቀፉ የፖሊሲ ምርምር ኢንስቲትዩት ተመራማሪ የሆኑት ታደሰ ዘርፉ (ዶ/ር) ናቸው፡፡

ስለ ጉዳዩ ያስረዱት የህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት አባል በስራችን ያሉ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች እነዚህን ጉዳዮች በአንድ ላይ አይሰሩም ከዚህ አንፃር የምንሰጣቸው ምክረ ሃሳቦች አይተገበሩም ይላሉ፡፡
ሁሉንም የችግሩ መንስኤዎች አካቶ የሚሰራ ባለሙያ ለማፍራት ካሪኩለሞችን መከለስ፣ስልጠናዎች መስጠት ያስፈልጋል የሚለው በጥናቱ በምክረ ሃሳብነት ቀርቧል፡

ተቋማት የአየር ንብረት ለውጥን፣ስርዓተ ምግብነረና ስርዓተ ፆታን እንዴት አስተሳስረው ይስሩ? የሚለውም ትኩረት ተሰጥቶታል ብለውናል ተመራማሪው ታደሰ ዘርፉ (ዶ/ር)፡፡
በፎረም ፎር ሶሻል ስተዲስ የጂካን ፕሮጀክት የተከወነው ጥናቱ በፖሊሲ ደረጃ ያሉ ችግሮችን ለመለየት የተከወነ ሲሆን ጥናቱን ምን ያህል እውነት ነው የሚለውን ለማወቅ ይመለከታቸዋል ካላቸው ተቋማት ጋር አጥኚው ተቋም ተወያይቷል፡፡
ምንታምር ፀጋው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
Telegram : https://t.me/ShegerFMRadio102_1
Facebook፡ https://web.facebook.com/Sheger102.1












Comments