top of page

ሚያዝያ 19፣2016 - ሴቶች ስለ ሀገራቸው ከወንዶች እኩል ድምፃቸውን ማሰማት አለባቸው ሲሉ ፕሬዚደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ተናገሩ

ሴቶች ስለራሳቸው ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ስለ ሀገራቸውም ከወንዶች እኩል ድምፃቸውን ማሰማት አለባቸው ሲሉ ፕሬዚደንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ተናገሩ፡፡


ፕሬዘዳንቷ ይህን የተናገሩት፤ ኢትዮጵያ ለማካሄድ ባሰበችው የሀገራዊ ምክክር የሴቶች ተሳትፎና ድርሻ ምን መሆን አለበት? በሚል ውይይት ላይ ነው፡፡


ውይይቱ አዲስ አበባ ሀይሌ ግራንድ ሆቴል እየተካሄደ ነው፡፡


ሴቶች ውሳኔ የሚሰጥባቸው ቦታዎች ላይ መኖራቸው ለሀገር ጥቅሙ ብዙ ነው ብለዋል ፕሬዚዳንቷ፡፡


''ሴቶች በሀገር ጉዳይ ላይ በየትኛውም መስክ ከወንዶች እኩል ድምፃቸውን ማሰማት ያለባቸውን ለቁጥር ወይም ለኮታ ሳይሆን ስለሚችሉ ነው ብለዋል'' ፕሬዘዳንቷ፡፡


ሴቶች መፍትሄ ማፈላለግ ላይ ድርሻቸው ከፍተኛ መሆኑንም ፕሬዘዳንቷ አንስተዋል፡፡


ይሁንና በሀገራችን በምክክርና በአገር ጉዳዮች ላይ የሴቶች ተሳትፎ እምብዛ አይደለም ብለዋል፡፡


ለዚህም ማሳያ የሰሜኑ ጦርነት በሰላም ለመፍታት በተደረገው ስምምነት ላይ ከሁለቱም ወገን አንድም ሴት አልነበረም ብለዋል ፕሬዘዳንቷ፡፡

ይሁንና ግን የሰሜኑ ጦርነት ከፍተኛ ጉዳት ያስከተለው በሴቶች እና ሕፃናት ላይ ነው ብለዋል፡፡


የሴቶች እና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ኤርጎጌ ተስፋዬ በበኩላቸው '' ሴቶችን በምክክሩ እንዲሳተፉ ማድረግ እና ድምፃቸውንም መስማት ያስፈልጋል'' ብለዋል፡፡


የሀገራዊ ምክክሩ ውጤታማ እንዲሆን ትርጉም ያለው የሴቶች ተሳትፎ መኖር እንዳለበት ሚኒስትሯ አስረድተዋል፡፡


በምክክሩ የሴቶች ድርሻ ከፍተኛ ከሆነ የአገረ መንግስት ግንባታ ይፋጠናል ዘላቂ ሰላምም ይሰፍናል ብለዋል፡፡


የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነር ፕሮፌሰር መስፍን አርአያ በበኩላቸው የምክክሩ ሂደት የሴቶች ሚና ከፍተኛ መሆኑን አስረድተዋል፡፡


በምክክሩ የሴቶች ሚና ከኮታና ከቁጥር የዘለለ የሀሳብ ተሳትፎ እንዲያደርጉ እየሰራን ነው ብለዋል፡፡


ምክክሩ የሴቶች ድምፅ ጎልቶ የሚሰማበት እና የሚደመጥበት ይሆናል ብለዋል፡፡


የሀገራዊ ምክክሩን የውይይት ብቻ ሳይሆን ሀሳብ የሚተገበርበት ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል ፕሬዘዳንት ሳህለወርቅ ባስተላለፉት መልዕክት፡፡


ያሬድ እንዳሻው


የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…


Telegram: @ShegerFMRadio102_1




bottom of page