top of page

የሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ለውይይት በቀረቡት ስምንቱም አጀንዳዎች ላይ በተጀመረው ምክክር ከስምምነት ተደርሶ ሊጠናቀቅ ይችላል የሚል እምነት እንደሌለውና፣ አንዳንድ አጀንዳዎች ለቀጣይ ትውልድ ሊተላለፉ እንደሚችሉ ዛሬ በሰጠው መግለጫ ተናግሯል።

  • 2 hours ago
  • 2 min read

ነሐሴ 4 2018


የሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን ለውይይት በቀረቡት ስምንቱም አጀንዳዎች ላይ በተጀመረው ምክክር ከስምምነት ተደርሶ ሊጠናቀቅ ይችላል የሚል እምነት እንደሌለውና፣ አንዳንድ አጀንዳዎች ለቀጣይ ትውልድ ሊተላለፉ እንደሚችሉ ዛሬ በሰጠው መግለጫ ተናግሯል።



የምክክር ኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር እየተካሄደ ባለው ምክክር «ሐሳቤ ካልተደመጠ ጥዬ እሄዳለሁ» ማለት ተገቢ አይደለም ብለዋል።


በስምንቱም አጀንዳዎች ላይ ባይሆንም በተወሰኑት አጀንዳዎች ላይ በእርግጠኝነት «ጥሩ» የምክረ ሐሳቦች ይዘን እንቀርባለን የሚል እምነት አለን ያሉት ዋና ኮሚሽነር መስፍን አርአያ (ፕ/ር)፣ አንዳንዶቹ ሊዘገዩ እንደሚችሉ አስረድተዋል።


ኮሚሽነሩ ይህን ያብራሩት የምክክሩን ሂደት አስመልክተው ዛሬ ነሐሴ 4 ቀን 2018 ዓ.ም ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ነው፡፡


እየተካሄደ ባለው ምክክር በሁሉም አጀንዳዎች ላይ የሚመክሩ ቡድኖች እኩል በተያዘላቸው ጊዜ እየሄዱ እንዳልሆነ ኮሚሽነሩ ጠቁመዋል።


«እስከ ነገ ከሰዓት ድረስ ግን ሁሉም ቡድኖች 500 አባላት ወዳሉት የቡድን ውይይት ያልፋሉ ብለን እንጠብቃለን» ሲሉም አክለዋል፡፡


በመካሄድ ላይ ባለው ምክክር በተለይ በፌደራል ከተሞች አጀንዳ ሥር በአዲስ አበባ ጉዳይ እየመከሩ ያሉ ተመካካሪዎች ዘንድ ከፍተኛ ክርክር መኖሩን ነግረውን ከዚህ ቀደም መዘገባችን ይታወሳል፡፡


ባለፈው ቅዳሜ ሌሎች ተመካካሪ ቡድኖች ያጠናቀሯቸውን አጀንዳዎች 500 አባላት ላሏቸው ቡድኖች ሲያቀርቡ፣ በአዲስ አበባ ሥር የሚመክሩ ተመካካሪዎች ግን «ከተማዋ የኦሮሚያ ዋና ከተማና መቀመጫ መሆኗ በሕገ መንግሥቱ ይደንገግልን» በሚሉና «ይህ በፍጹም መሆን የለበትም» በሚሉ ተመካካሪዎች መካከል አለመስማማት በመፈጠሩ ለሌላ ቀን ቀጥረው ተበትነው ነበር፡፡


በከተማዋ ጉዳይ የሚመክሩ ተመካካሪዎች ጉዳዩ በጣም አከራካሪ መሆኑን ተናግረው፣ በቅርቡ ይጠናቀቃል የሚል እምነት እንደሌላቸው አስረድተዋል፡፡


አንዳንዶች የከተማዋ ጉዳይ ቢዘገይ ይሻላል የሚል እምነት እንዳላቸው የጉዳዩ ተመካካሪዎች ጠቅሰዋል፡፡


የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር መስፍን አርአያ (ፕ/ር) በበኩላቸው ዛሬ በሰጡት መግለጫ «እየተካሄደ ባለው ምክክር “ሐሳቤ ካልተደመጠ ጥዬ እሄዳለሁ” ማለት ተገቢ አይደለም። የምክክር ባህል ስለሌለን አንዳንዶቻችን አቋማችንን በጉልበትም ጭምር ነው ወደፊት ማምጣት የምንፈልገው» ካሉ በኋላ፣ «'ይህ ካልተደረገልኝ ይህን አደርጋለሁ'፣ 'ካልሰማኸኝ ጥዬህ እሄዳለሁ' ማለት ተገቢ አይደለም፤ እዚህ የመጣነው ጥሎ ለመሄድ አይደለም» ብለዋል፡፡


«እዚህ ስንመጣ አቋማችንንና አስተሳሰባችንን ከሌሎች ጓደኞቻችን፣ እህት ወንድሞቻችንና ወላጆቻችን ጋር ወደ ማህል በማምጣት ሁላችንም አሸናፊ እንድንሆን ነው» ሲሉ አብራርተዋል፡፡ እንደ ኮሚሽነሩ ማብራሪያ፣ «አሸናፊ ሆኖ ለመውጣት ነው 'ካልሰማኸኝ ጥዬ እወጣለሁ' የሚባለው።»


«በስምንቱም ባይሆንም በተወሰኑት አጀንዳዎች ላይ በእርግጠኝነት ጥሩ የምክረ ሐሳቦች ይዘን እንቀርባለን የሚል ተስፋ አለን» ያሉት ዋና ኮሚሽነሩ፣ «ቢቻል በአብዛኞቹ ላይ፣ ወይም በሁሉም ላይ፤ አለበለዚያ ግን የተወሰኑት አጀንዳዎች ሊያድሩ ይችላሉ፤ የተወሰኑት ግን ሊፈቱ ይችላሉ።


ሁሉንም ማለትም ስምንቱንም ጨርሰን እንወጣለን የሚል እምነት የለንም፤ አንዳንዶች ጊዜ ይፈጃሉ» ሲሉ አስረድተዋል፡፡


ኮሚሽነሩ የትኞቹ አጀንዳዎች ሊዘገዩ አንደሚችሉ ወይንም በየትኞቹ አጀንዳዎች ላይ ከስምምነት ተደርሶ ምክረ ሀሳብ ሊሰጥ እንደሚችል በመገለጫቸው ያሉት ነገር የለም፡፡


ኮሚሽነሩ በመግለጫቸው «እዚህ የመጣነው ከየመንደራችን ይዘን የመጣነውን ጥያቄ ለመመለስ አይደለም፤ እዚህ የመጣነው ሀገራችንን ኢትዮጵያን ማዕከል አድርገን መሆን አለበት» ሲሉ ለተሳታፊዎች፣ ለአስተባባሪዎች እንዲሁም በምክክሩ ላይ ለነበሩ አካላት መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡


«እስካሁን ድረስ አንድም ውሳኔ በአንድም አጀንዳ ላይ አልተሰጠም፤ ምናልባትም ወደፊትም አይሰጥም፣ የሚሰጠው ምክረ ሐሳብ ነው» ብለዋል ዋና ኮሚሽነር መስፍን አርአያ (ፕ/ር)፡፡


ያሬድ እንዳሻው

Recent Posts

See All
የነሐሴ 4 2018 የውጪ ሀገር ወሬዎች

#ሳውዲ_አረቢያ በሳውዲ አረቢያ ጂዛን በሚገኝ የነዳጅ ማጣሪያ ላይ ከባድ ቃጠሎ ተቅስቅሶ ነበር ተባለ፡፡ በጂዛኑ ማጣሪያ ላይ ቃጠሎ ተቅስቅሶ የነበረው ከባድ ፍንዳታ ከተሰማ በኋላ እንደሆነ አናዶሉ ፅፏል፡፡ በጁቢየል የተፈጥሮ ጋዝ ማሰናጃ ከተማም ቃጠሎ ተቀስቅሶ ነበር ተብሏል፡፡ የሳውዲ ምንጮች ቃጠሎዎቹ ተቀስቅሰው እ

 
 
 
በሆነውም ባልሆነውም እየተቀጣን ነው ሲሉ አሽከርካሪዎች ያማርራሉ፡፡

ነሐሴ 4 2018 በሆነውም ባልሆነውም እየተቀጣን ነው ሲሉ አሽከርካሪዎች ያማርራሉ፡፡ የአዲስ አበባ ትራፊክ ማኔጅመንት በበኩሉ ሳያጠፋ የምንቀጣው አሽከርካሪ የለም እንዲያውም ሁሉንም ህጎች እናስከብር ብንል የማይቀጣ አሽከርካሪ አይኖርም ብሏል፡፡ ሙሉ ዘገባውን ያድምጡ.... ምህረት ስዩም

 
 
 

Comments


Sheger App Logo
iOS Store
Google Play
  • Facebook
  • X
  • Youtube
  • TikTok
  • Telegram
  • Whatsapp

    ሸገር
102.1

ሸገር ኤፍ ኤም 102.1 አዲስ የሬዲዮ አቀራረብ መላና አዲስ ቃና ይዞ የቀረበ በሀገሪቱ የሚዲያ ገበያ ላይ መሪ ሚና የሚጫወት ጣቢያ ነው፡፡

ሁሌም ከሸገር ጋር ሁኑ
ሸገር የእናንተ ነው
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር! 

Sheger Radio | Sheger 102.1FM  © 2026 Adey Tensae Media & Entertainment PLC.  

bottom of page