top of page

ሚያዝያ 18፣2016 - ''የፀጥታ ችግር በምርት አቅርቦቱ ላይ ምንም ዓይነት ተፅህኖ አላሳደረብኝም'' የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ

በሀገሪቱ ባለው የፀጥታ ችግር ምክንያት በምርት አቅርቦቱ ላይ ምንም ዓይነት ተፅህኖ አላሳደረብኝም ሲል የአዲስ አበባ ንግድ ቢሮ ተናገረ፡፡


በበዓላት ሰሞን ወደ ከተማው የሚገቡ የቁም እንስሳት ከተለያዩ ቦታዎች በሰፊው እየገቡ ነው ሲልም ቢሮው አስረድቷል፡፡


በፀጥታውም ሆነ በትራንስፖርት ችግር ምክንያት የአቅርቦቱ ቁጥር አላነሰም፤ በአንፃሩም የአቅርቦት መጠን እየጨመረ መጥቷል ብሏል ቢሮው፡፡


ይህ የተባለው የትንሳኤን በዓል ገበያ ለማረጋጋት ቅድመ ዝግጅትን በተመለከተ ቢሮው በሰጠው መግለጫ ላይ ነው፡፡


መጪውን የትንሳኤ በዓል ምክንያት በማድረግም ቢሮው በምርት አቅርቦት፣ ሕገወጥ የንግድ እንቅስቃሴዎችን በመወቆጣጠር ረገድ ለበአሉ የተለየ እቅድ በማቀድ በቢሮው ሀላፊ የሚመራ ግብረ ሀይል ተቋቁሞ ወደ ስራ መግባቱንም ሰምተናል፡፡


ለበዓሉም በ188 የእሁድ ገበያዎች ሰፊ የምርት አቅርቦት እንዲፈጠር በማድረግ በመደበኛነት ቅዳሜና እሁድ የሚካሄደው የእሁድ ገበያ ሳምንቱን ሙሉ እንዲካሄድ በማስቻል ህብረተሰቡ በአቅራቢያው የሚያስፈልገውን ምርት ማግኘት የሚቻልበትን እድልም ፈጥረናል ብሏል ቢሮው፡፡

በህገወጥ ንግድ እንቅስቃሴ የተሰማሩ ነጋዴዎች እርምጃ እንደተወሰደባቸውም ሰምተናል፡፡


የዋጋ ንረቱም ከማረጋጋት አኳያም ከ15 እስከ 20 ፐርሰንት ቅናሽ የተደረገባቸው ምርቶችም በእሁድ ገበያ በሰፊው ለህብረተሰቡ በማቅረብ በገበያው ላይ መሻሻሎች ታይተውበታል ተብሏል፡፡


የባዛርና የንግድ ትርዒት በመክፈት ለበዓል ገበያው ተደራሽ ለማድረግ እንቅስቃሴ እያደረግን ነው ብሏል ቢሮው፡፡


ከዚህ ቀደም የቢሮው ሀላፊዎች ሆኑ ሌሎች ሹመኞች በያካባቢው ያለው የፀጥታ ችግር ወደ ከተማዋ በሚገቡ የምርት አቅርቦት ላይ ችግር ፈጥሯል ብለው ሲናገሩ እንደነበር ይታወሳል፡፡


ፍቅሩ አምባቸው


የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…


Telegram: @ShegerFMRadio102_1




bottom of page