top of page

መጋቢት 11፣2016 - ከፕሮጀክቶች ካሳ ጋር የተያያዙ ክሶች ክርክር የሚደረገው በፌዴራል የመጀመሪያ ፍርድ ቤት ብቻ ይሆናል ተባለ

  • sheger1021fm
  • Mar 20, 2024
  • 1 min read

በክልሎችም ሆነ በከተማ አስተዳደሮች የፌዴራል መንግስት የሚገነባቸው ፕሮጀክቶች በተመለከተ ከልማት ተነሺ ካሳ ጋር የተያያዙ ክሶች ክርክር የሚደረገው በፌዴራል የመጀመሪያ ፍርድ ቤት ብቻ ይሆናል ተባለ፡፡


ተሻሽሎ ለህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት በቀረበው ለህዝብ ጥቅም ሲባል የመሬት ይዞታ የሚለቀቅበትን፣ ካሣ የሚከፈልበትን እና ተነሺዎች መልሰው የሚቋቋሙበትን ሁኔታ የሚመለከተው ረቂቅ አዋጅ፤ የፍርድ ቤት ክርክሮች በፌዴራል ፍርድ ቤት ብቻ እንዲሆን የሚደነግግ ነው፡፡


እንደ መንገድ፣ የባቡር መስመር ዝርጋታ፣ የኤልክትሪክና መሰል ስራዎች በፌዴራል መንግስት ተቋም ስለሚገነቡ ፕሮጀክቱ የሚተገበረው በክልል ቢሆንም ቅሬታ ያለው ሰው በፍርድ ቤት መከራከር ከፈለገ በፌዴራል ፍርድ ቤት ብቻ እንዲሆን ህጉ ያስገድዳል፡፡


ከዚህ ቀደም በነበረው ፕሮጀክቶቹ በሚገነቡባቸው አካባቢዎች ባሉ ፍርድ ቤቶች ክርክር ማድረግ ይቻል የነበረ ሲሆን በአዲሱ ረቂቅ ሃላፊነቱ ለፌዴራል የመጀመሪያ ፍርድ ቤት ተሰጥቷል፡፡


በዚህም ምክንያት ከንብረት ካሣ፣ ከልማት ተነሺዎች ድጋፍ ከኢኮኖሚ ጉዳት ካሣ፣ የማህበራዊ ትስስር መቋረጥ እና የስነ ልቦና ጉዳት ካሣ ጋር ተያይዞ በፍርድ ቤት መከራከር የሚፈልጉትን ሁሉ ካሉበት ክልል ወደ ፌዴራል መጥተው አቤት እንዲሉ በረቂቁ ተደንግጓል፡፡


በተጨማሪም በተለይ በፍርድ ቤት ከሚደረጉ ክርክሮች ጋር በተያያዘ በፍርድ ቤቶች የሚሰጡ ጊዜያዊ ትዕዛዝም ከፍርድ ቤቱ ፕሬዘዳንት እውቅና ውጭ ተፈፃሚ መሆን አይችሉም ተብሏል፡፡


በተለይ የፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ የፌዴራል መንግስት ተቋምን የባንክ ሂሳብ የማገድ ወይም ከአፈፃፀም ጋር በተያያዘ ከፍተኛ አመራሮች ተገደው ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ የሚሰጡ የፍርድ ቤት ትዕዛዞች ከፌዴራሉ የመጀመሪያ ፍርድ ቤት ፕሬዘዳንት እውቅና ሳይሰጡ ተፈፃሚ እንደማይሆን ከረቂቅ አዋጁ ላይ ተመልክተናል፡፡


ትዕግስት ዘሪሁን


የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…




Comments


Sheger App Logo
iOS Store
Google Play

    ሸገር
102.1

ሸገር ኤፍ ኤም 102.1 አዲስ የሬዲዮ አቀራረብ መላና አዲስ ቃና ይዞ የቀረበ በሀገሪቱ የሚዲያ ገበያ ላይ መሪ ሚና የሚጫወት ጣቢያ ነው፡፡

ሁሌም ከሸገር ጋር ሁኑ
ሸገር የእናንተ ነው
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር! 

Sheger Radio | Sheger 102.1FM  © 2025 Adey Tensae Media & Entertainment PLC.  

bottom of page