መስከረም 20 2018 - የውጪ ሀገራት ወሬዎች
- sheger1021fm
- Sep 30
- 2 min read

የአሜሪካው ፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ የጋዛ የሰላም እቅድ በአውሮፓ እና በመካከለኛው ምስራቅ የብዙ አገሮችን ድጋፍ እያገኘ ነው ተባለ፡፡
እቅዱ ትራምፕ እና የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታንያሁ እንደተስማሙበት ቢቢሲ ፅፏል፡፡
በእቅዱ መሰረት ሐማስ በእጁ የሚገኙ እስራኤላዊን ታጋቾች እና የሟች ታጋቾችን አስከሬን በሙሉ ይለቃል፡፡
ታጣቂ ቡድኑም ትጥቅ እንዲፈታ ይጠይቃል የሰላም እቅዱ፡፡
ሐማስ እቅዱን ሙሉ በሙሉ መቀበሉ እንደተረጋገጠ የተኩስ አቁም ተደርጎ የእስራኤል ጦር ደረጃ በደረጃ ከጋዛ እንዲወጣ ይደረጋል፡፡
የፕሬዘዳንት ማሐሙድ አባስ መንግስት በዚህ ጉዳይ ከአሜሪካ ጋር ለመተባበር ዝግጁ ነኝ ማለቱ ተሰምቷል፡፡
በርካታ የመካከለኛው ምስራቅ እና የአውሮፓ አገሮች ለእቅዱ ድጋፋቸውን እየሰጡ ነው ተብሏል፡፡

#ደቡብሱዳን
በደቡብ ሱዳን ወሰን ጥይት ሲሸጡ ተደርሶባቸዋል የተባሉ 5 የኬኒያ የፖሊስ መኮንኖች ተይዘው ታሰሩ፡፡
መኮንኖቹ በደቡብ ሱዳን ወሰን አንድ የገበያ ስፍራ ሊሸጧቸው እንደተሰናዱ የተያዙት ጥይቶች በናይሮቢ ከሚገኘው ማዕከላዊ ግምጃ ቤት የወጡ ናቸው መባሉን ቱኮ ፅፏል፡፡
የተያዙበት የገበያ ስፍራም በህገ-ወጥ ግብይት የታወቀ ቦታ እንደሆነ ተጠቅሷል፡፡
በዚሁ ህገ-ወጥ የጥይት ንግድ ንክኪ ያላቸው ሌሎች ተጠርጣሪዎችም አሉ ተብሏል፡፡
የህገ ወጡ የጥይት ንግድ ጉዳይ ከበድ ያለ ምርመራ መቀጠሉ ታውቋል፡፡

አሜሪካ ለዩክሬይን በረጅም ርቀት ተወንጫፊ ሚሳየሎች የማስታጠቁን ጉዳይ እያሰበችበት እንደሆነ ምክትል ፕሬዘዳንት ጄ ዲ ቫንስ ተናገሩ፡፡
ቫንስ አሜሪካ ቶም ሐውክ የተሰኙትን ረጅም ርቀት ተወንጫፊ ሚሳየሎች ለዩክሬይን ልታስታጥቃት እንደምትችል ፍንጭ መስጠታቸውን ቢቢሲ ፅፏል፡፡
በዚህ ጉዳይ የመጨረሻው ውሳኔ የሚጠበቀው ከፕሬዘዳንት ዶናልድ ትራምፕ እንደሆነ ምክትል ፕሬዘዳንቱ ተናግረዋል፡፡
ትራምፕ ከዚህ ቀደም በእለት አስቆመዋለሁ ያሉት ጦርነት እንዳሰቡት ስላልሆነላቸው በአሁኑ ወቅት የአቋም ለውጥ እያደረጉ ነው ይባላል፡፡
ቶም ሐውክ ሚሳየሎች እስከ 2 ሺህ 500 ኪሎ ሜትር የመምዘግዘግ አቅም ያላቸው ናቸው፡፡
የሩሲያው መንግስታዊ ቃል አቀባይ ምንም ይምጣ ምን በጦርነት ይዞታ እና አሰላለፋችን ላይ የሚያስከትለው ለውጥ አይኖርም ማለታቸው ተጠቅሷል፡፡

ፊሊፒንስ እና ቬየትናምን የመታ ከባድ አውሎ ነፋስ ከ30 በላይ ሰዎችን ገደለ ተባለ፡፡
አውሎ ነፋሱ በፊሊፒንስ 24 ሰዎችን መግደሉን የአገሪቱ ሹሞች እንደተናገሩ AFP ፅፏል፡፡
ቡአሎይ የተሰኘው አውሎ ነፋስ በቬየትናምም 11 ሰዎችን መግደሉ ተሰምቷል፡፡
አውሎ ነፋሱ ቬየትናም ሲደርስ በሰዓት 130 ኪሎ ሜትር በሆነ ፍጥነት ሲጋልብ ነበር ተብሏል፡፡
በብዙ ሺህዎች በሚቆጠሩ ቤቶች ላይ ጉዳት ማድረሱ ታውቋል፡፡
ከቤቶች እና ሕንፃዎችላይ ቆርቆሮዎችን እየነቃቀለ ወስዷል ተብሏል፡፡
የAFP ጋዜጠኞችም ይሄንን በስፍራው በዓይናችን በብርቱ አይተናል የሚል ምስክርነት ሰጥተዋል፡፡
በዚህ የእስያ ክፍል ለአውሎ ነፋሱ ድግግሞች መጨመር የአየር ለውጡ በዋና ምክንያትነት እየቀረበ ነው፡፡

ኢራን በእስራኤል አንዳች ጥቃት እንዳይሰነዘርባት በብርቱ አስጠነቀቀች ተባለ፡፡
ኢራን አንዳች ጥቃት የሚሰነዘርባት ከሆነ ከእስራኤል ጋር ወደ ሙሉ ጦርነት እንደምትገባ ያስጠነቀቁት አብዮታዊ ዘብ የተሰኘው የኢራን የጦር ክፍል የቀድሞ ሜጄር ጄኔራል እንደሆኑ ዘ ቴሌግራፍ ፅፏል፡፡
ጦርነቱ አንዴ ከተቀሰቀሰ በአካባቢው የሚገኙ የአሜሪካ ተቋማትንም አናስተርፋቸውም ብለዋል ነባሩ የጦር መኮንን፡፡
ኢራን በኒኩሊየር መርሐ ግብሯ ምክንያት አለም አቀፋዊው ማዕቀብ ከ10 አመታት በኋላ መልሶ ከተጣለባት በኋላ እስራኤልም በኢራን ልጠቃ እችላለሁ የሚል ስጋት እንደገባት ይነገራል፡፡
ባለፈው አመት ሰኔ ወር ኢራን ከእስራኤል ጋር በከባድ ግጭት ውስጥ መሰንበታን መረጃው አስታውሷል፡፡
አሁንም በቀጠና ዳግም ውጥረት መንገሱ እየተሰማ ነው፡፡ የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
Comments