የኢትዮጵያን የተቆላ ቡና በኢ-ኮሜርስ ንግድ ለአለም ገበያ ማቅረብ የሚቻልበት የንግድ መድረክ ዛሬ ስራ መጀመሩ ተነገረ፡፡
- Jul 22
- 2 min read
ሐምሌ 15 2018
የኢትዮጵያን የተቆላ ቡና በኢ-ኮሜርስ ንግድ ለአለም ገበያ ማቅረብ የሚቻልበት የንግድ መድረክ ዛሬ ስራ መጀመሩ ተነገረ፡፡
ይህ አዲስ መድረክ በአለም ዙሪያ ያሉ ቡና ወዳጆች የኢትዮጵያን የተቆላ ቡና ባሉበት ቦታ ሆነው በኦንላይን በማዘዝ በጥቂት ቀናት ውስጥ መረከብ እንዲችሉ የሚያደርግ ነው ተብሏል፡፡

ዛሬ በሃያት ሪጀንሲ ሆቴል በተካሄደ ዝግጅት ዲ.ኤች.አል ኤክስፕረስ ኢትዮጵያ እና ኢ.ኤክስ.ኤም ግሎባል ኃላ.የተ.የግ.ማህበር የኢ-ኮሜርስ የውጭ ንግድ መድረኩ መጀመሩን ይፋ አድርገዋል፡፡
ዲጂታል የግብይት መድረኩ አስር የኢትዮጵያ የቡና ብራንዶችን ይዞ ስራ የጀመረ ሲሆን ለግል መጠቀሚያ የሚሆኑ ስፔሻሊቲ ትዕዛዞችን እንዲሁም ከፍተኛ መጠን ያለው ትዕዛዝን ለመፈፀም ያስችላል ተብሏል፡፡
ይህ የተለያየ የኢትዮጵያን የተቆላ የቡና ብራንድ በአንድ መድረክ ለገበያ ለማቅረብ ያስችላል የተባለለት ሥርዓት በኢትዮጵያ የመጀመሪያው መሆኑ ተነግሯል።
በኢትዮጵያ ገበያ ቡና ቆልተው የሚያቀርቡ ተቋሞች ያለ ድካም ወደ አለም አቀፍ ገበያ በቀላሉ ለመግባት እንዲችሉ ያደርጋል ተብሏል፡፡
ስራውም የዲጂታል ንግድን ፣ የጥራት ማረጋገጫን ፣ የህግና ደንብ ተገዥነትን እና አለም አቀፍ ደረጃን በጠበቀ መንገድ እንደሚከወን ተነግሯል፡፡
በቢዝነስ ስምምነቱ መሰረት ኢ.ኤክስ.ኤም ግሎባል የገበያ መድረኩን የአቅራቢዎች ምዝገባን የጥራት ማረጋገጫ ቅንጅትን እንዲሁም የደንብ ተገዢነት ሂደት ስራን ይመራል ተብሏል፡፡
ሌላኛው አጋር ዲ.ኤች.ኤል ኤክስፕረስ ኢትዮጵያ ደግሞ ከጫፍ እስከ ጫፍ ያለውን አለም አቀፍ የሎጀስቲክስ አገልግሎት ፣ የጉምሩክ ሂደትን እንዲሁም በአለም ዙሪያ ትዕዛዙን የማድረስ ሀላፊነትን እንደሚወጣ ተነግሯል፡፡
የኢ.ኤክስ.ኤም ግሎባል ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ ኢምራን ኑርሁሴን ይህ የኦንላየን የግብይት መድረክ በኢትዮጵያ ቡናን ቆልተውና አሽገው በሚልኩና፣ የኢትዮጵያ ቡና ወዳጅ በሆኑ ገዢዎች መሀከል ድልድይ የሚሆን ነው ብለዋል፡፡
የዲ.ኤች.ኤል ኤክስፕረስ ኢትዮጵያ ዋና ስራ አስኪያጅ ዲርክ ቫን ዶርን ይህ ዲጂታል የንግድ ሥርዓት የወጪ ንግድ ተወዳዳሪነትን ለማሳደግ ፣ እሴት የተጨመረበት የግብርና ምርት ኤክስፖርትን ለማሳደግ የሚደረገውን ሀገራዊ ጥረትን የማያግዝ ነው ብለዋል፡፡
ኢ.ኤክስ.ኤም ግሎባል ከውጭ ንግድ ጋር የተገናኙ መረጃዎችን የመተንተን እና የደንብ ተገዢነትን በተመለከተ የስራ ዘርፍ የተሰማራ የዲጂታል መድረክ መሆኑ ተወርቷል፡፡
ሌላኛው መስራች ተቋም ዲ.ኤች.ኤል አለም አቀፍ የሎጅስቲክስ ኩባንያ ሲሆን ዲ.ኤች.ኤል ኤክስፕሪስ ደግሞ የዲ.ኤች.ኤል ግሩፕ አካል መሆኑ ተነግሯል፡፡
ቴዎድሮስ ወርቁ
_edited.jpg)


Comments