የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓመቱ 9.1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን ተናገረ።
- 3 hours ago
- 1 min read
ሐምሌ 22 2018
የኢትዮጵያ አየር መንገድ በዓመቱ 9.1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን ተናገረ።
የሆርሙዝ ሰርጥ መዘጋት ለስራው እንቅፋት እንደነበርና የመካከለኛው ምስራቅ ጦርነት በዚህ ከቀጠለ ትርፋማነቱን ሊቀንሰው እንደሚችል ጠቅሷል።

አየር መንገዱ የ2018 ዓመት አፈፃፀሙን አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጠው መግለጫ በዓመቱ 9.1 ቢሊዮን የአሜሪካን ዶላር ማግኘቱንና ገቢው ከአምናው ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲመሳከር የ20 በመቶ እድገት እንዳለው ተናግሯል።
ሆኖም ግን በመካከለኛው ምስራቅ በነበረው ጦርነት ምክንያት የበረራዎች እቀባ ስለነበር ተጓዦችንም ሆነ ጭነት ማጓጓዝ ባለመቻሉ የእቅዱን 96 ከመቶ እንዲፈፅም ምክንያት እንደሆነው የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ መስፍን ጣሰው አስረድተዋል።
በጦርነቱ ምክንያት የነዳጅ ዋጋ በመጨመሩ አየር መንገዱ ወጪው በ25 በመቶ ጨምሯል ያሉት ዋና ስራ አስፈፃሚው አቶ መስፍን አሁንም ጦርነቱ ቀጥሏል፤ የነዳጅ ዋጋም እየጨመረ ነው፤ በዚሁ ከቀጠለ ትርፋማነቱ ላይ ችግር ሊፈጥር እንደሚችልም ጠቁመዋል።
አየር መንገዱ በዓመቱ 20.7 ሚሊዮን መንገደኞችንና 897 ሺህ ቶን ጭነት በማጓጓዝ አለም አቀፍ መዳረሻዎቹን 150 የሃገር ውስጡን ደግሞ 25 ማድረሱንና በዚህም በኩል ከ8 እስከ 16 በመቶ እድገት እንዳለ አቶ መስፍን ተናግረዋል።
በመጪው ዓመት የመንገደኞችን ቁጥር 23 ሚሊዮን ገቢውንም 10 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ ውጥን መያዙን ያነሱት አቶ መስፍን ተጨማሪ 6 ዓለም አቀፍ መዳረሻዎችንና 17 አዳዲስ አውሮፕላኖች በግዢ ሂደት ላይ መሆናቸውንም የአየር መንገድ ግሩፕ ዋና ስራ አስፈፃሚው አቶ መስፍን ጣሰው በመግለጫቸው ጠቅሰዋል።
ምንታምር ጸጋው
_edited.jpg)
