በሕገ-ወጥ መንገድ ሰዎችን ወደ ስደት ልከዋል፣ ከተጎጂዎችም ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ተቀብለዋል ተብለው በተጠረጠሩ 16 ሰዎች ላይ ብይን ለመስጠት ፍርድ ቤት ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።
- 22 hours ago
- 2 min read
ሐምሌ 22 2018
በሕገ-ወጥ መንገድ ሰዎችን ወደ ስደት ልከዋል፣ ከተጎጂዎችም ከአንድ ቢሊዮን ብር በላይ ተቀብለዋል ተብለው በተጠረጠሩ 16 ሰዎች ላይ ብይን ለመስጠት ፍርድ ቤት ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።

በአደገኛ ሕገወጥ ሰው አዘዋዋሪነት ተጠርጥረው በፖሊስ ተይዘው ክስ የተመሠረተባቸው 16 ተከሳሾች ዛሬ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ ችሎት ቀርበው ክሳቸው ተሰምቷል።
ተጠርጣሪዎቹ በሰው ልጅ ለመነገድ በማሰብ የወንጀል ቡድን በማደራጀት፣ የሕገወጥ ሰዎች ዝውውር መረብ በመዘርጋት እንዲሁም ተጎጂዎቹ በየመን በኩል ወደ ሳዑዲ ዓረቢያ ገብተው የተሻለ ኑሮ እንደሚኖሩ ሐሰተኛ ተስፋ በመስጠትና በማሳመን ከተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች በመመልመል ሲልኩ እንደነበር በአቃቤ ሕግ የክስ መዝገብ ተጠቅሷል።
በሕገወጥ መንገድ የተወሰዱ ተጎጂዎች የኢትዮጵያን ድንበር እንደተሻገሩ ወደ ጅቡቲ ተወስደው፣ በየመን ሀገር በሚገኙ ለዚሁ ዓላማ በተዘጋጁ መጋዘኖች ታጉረው ከፍተኛ ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶች ይፈጸሙባቸው እንደነበር በክሱ ተብራርቷል።
ተጠርጣሪዎቹ ተጎጂዎችን ወደ ቤተሰቦቻቸው ስልክ በማስደወል ከፍተኛ ገንዘብ ሲጠይቁ እንደነበር እና ገንዘብ መክፈል ላልቻሉ ቤተሰቦች ተጎጂዎችን እየደበደቡ፣ እንዲሁም እያሰቃዩ ቪዲዮ በመቅረጽ የሥነልቦና ጫና ሲፈጥሩ እንደነበርም ተረጋግጧል ይላል የአቃቤ ሕግ ክስ።
በዚህ መልኩ ከተጎጂዎች ከ1 ቢሊዮን ብር በላይ በሕገ-ወጥ መንገድ መሰብሰባቸውን፣ ከ40,000 በላይ ሰዎችን በሕገ-ወጥ መንገድ ማዘዋወራቸውን፣ በሂደቱም ከ60 በላይ ሰዎች እንደሞቱ እንዲሁም በርካታ ሴቶች መደፈራቸውን በአቃቤ ሕግ የክስ መዝገብ ሰፍሯል።
አቃቤ ህግ በጠርጣሪዎቹ ላይ በሰው የመነገድ፣ በሕገ-ወጥ ሐዋላ እና በሕገ-ወጥ የገንዘብ ዝውውር (Money Laundering) በሚሉት 6 የክስ መዝገቦች ክስ አቅርቦባቸዋል፡፡
በዚህ መሠረት የ61 ሰዎች ሕይወት አልፏል፤ የ13 እና የ15 ዓመት ሕፃናትን ጨምሮ የ10 ሰዎች ደግሞ ደብዛቸው ጠፍቷል፤ ተደፍረው ያረገዙ ሴቶችም አሉ ሲል አቃቤ ሕግ ዛሬ ለችሎቱ አስረድቷል።
ተከሳሾቹ የዋስትና መብታቸው ቢከበርላቸው ከሀገር ሊወጡ ይችላሉ ሲልም የዋስትና መብታቸው ተከብሮ ከእስር እንዳይለቀቁ ጠይቋል፡፡
በተጨማሪም የተከሰሱበት ወንጀል ተደራራቢና ሦስቱም የክስ መዝገቦች ከ15 እስከ 25 ዓመት የሚያስቀጡ በመሆናቸው የዋስትና መብታቸው ቢከበርላቸው ዋስትናውን አክብረው ሊገኙ ስለማይችሉ ሊከለከሉ ይገባል ሲልም አስረድቷል፡፡
የተከሳሽ ጠበቆች በበኩላቸው ተከሳሾች ቋሚ የመኖሪያ አድራሻ ያላቸውና ቤተሰብ የመሠረቱ በመሆናቸው የዋስትና መብታቸውን አክብረው አይገኙም የሚለው የአቃቤ ሕግ ሀሳብ የሕግ መሠረት የለውም ሲሉ ተከራክረዋል።
በተደራራቢ ወንጀል ቢከሰሱም የዋስትና መብት ግዙፍ ሕገመንግሥታዊና ሰብአዊ መብት በመሆኑ ሊከለከል አይገባውም ሲሉም ለችሎቱ አመልክተዋል።
የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ወንጀል ምድብ ችሎት መዝገቡን መርምሮ በዋስትና ክርክሩ ላይ ብይን ለመስጠት ለሐምሌ 30 ቀን 2018 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ሰጥቷል።
የፌዴራል ፖሊስ በአደገኛ ሕገወጥ አዘዋዋሪ መሐመድ ጣሂር አደን (ወርዲ) የሚመሩ 17 የተደራጁ የወንጀል ቡድን አባላትን በቁጥጥር ሥር አውሎ የምርመራ መዝገብ በሰውና በሰነድ ማስረጃ በማደራጀት ክስ ይመሠረትባቸው ዘንድ ለፍትሕ ሚኒስቴር መላኩን መናገሩን ይታወሳል።
ገዛ ጌታሁን
_edited.jpg)
