top of page

''የአቪየሽን ሴኩሪቲ አዋጅ ተገልጋዩን ጫና ውስጥ የሚከትት ነው" የፓርላማ አባል

  • 1 day ago
  • 2 min read

ሚያዝያ 13/ 2018


ተጨማሪ የአቭየሽን ክፍያ መክፈልን የሚያስገድደው የአቪየሽን ሴኩሪቲ አዋጅ ተገልጋዩን ጫና ውስጥ የሚከትት፤የሃገሪቱን የፋይናንስ ስርዓት የሚጥስ ነው፤ በሚል በፓርላማው ጥያቄ አስነሳ፡፡


አዋጁ በስራ ላይበ ሲውል እያንዳንዱ የአየር መንገድ ተጓዥ ከ30 እስከ 156 ብር የደረሰ ተጨማሪ ክፍያ የሚጠየቅበትን አሰራር የሚዘረጋ ነው፡፡


የህዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት ዛሬ ባካሄደው መደበኛ ስብሰባው ላለፉት 20 ዓመታት ሲሰራበት የቆየውን ነባሩን የአቪየሽን ሴኩሪቲ አዋጅ ለማሻሻል በውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዮች ቋሚ ኮሚቴና በከተማ መሰረተልማትና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ በቀረበለት የረቂቅ አዋጁ ሪፖርትና የውሳኔ ሀሳብ ላይ ተወያይቷል፡፡


በዚህም ወቅት በአዋጁ የተለያዩ ድንጋጌዎች ላይ ከፓርላማ አባላት ጥያቄዎች ተነስተዋል፡፡


የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ከራሱ መንገደኞች፣ ከሌሎች ኦፕሬተሮች እና በኤርፖርት ውስጥ የአቪዬሽን ሴኪዩሪቲ አገልግሎት ከሚያገኙ ማናቸውም አካላት የአገልግሎት ክፍያ በመሰብሰብ፤ ለብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ገቢ እንዲያደርግ የሚያዘው የአዋጁ ክፍል ላይ የተነሳው ጥያቄ አንዱ ነው፤ የፓርላማ አባሉ ክፍያው ተጓዦች ለቲኬት በሚያወጡት ወጪ ላይ ተጨማሪ ስለሚሆን ማህበረሰቡን የኢኮኖሚ ጫና ውስጥ የሚከት ነው፤አየር መንገዱ አትራፊ ድርጅት ሆኖ እዚህ ክፍያው ውስጥ መግባቱ ተገቢ አይደለም ብለዋል፡፡



የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዮች ቋሚ ኮሚቴ ምክትል ሰብሳቢ ዶክተር ተኪ ማህዲ ለተነሱ ጥያቄዎች በሰጡት ምላሽ የብሄራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ማቋቋሚያ አዋጅ ተቋሙ ለሚሰጠው አገልግሎት ክፍያ እንዲቀበል ይፈቅድለታል፤በዚህ የሴኩሪቲ አዋጅ ደግሞ አንዱ ፈጻሚ አካል መሆኑ ገቢውን እንዲሰበስብ ያስችለዋል ብለዋል፡፡


በተጨማሪም የክፍያውን ተገቢነት ለማስረዳት አለም አቀፍ አሰራርን ይጠቅሳሉ የአለም አቀፍ ሲቪል አቪየሽን ድርጅት አየር መንገዶች ለመንገደኞችና ለእቃዎቻቸው ደህንነት መጠበቅ ለሰጡት አገልግሎት እንዲያስከፍሉ ያዛል ኢትዮጵያም የድርጅቱ አባል በመሆኗ ወደዚህ አሰራር ገብታለች ሲሉ አስረድተዋል፡፡


ሌላኛው የፓርላማ አባልም ከተጓዡ እንዲህ አይነት ተጨማሪ ገንዘብ መሰብሰብ ተገቢ አለመሆኑን በማንሳት አሰባሰቡም በኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ተሰብስቦ ለብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ገቢ መሆኑ ተገቢ አይደለም፤ እነዚህ ተቋማት ፓርላማው በበጀት የሚያስተዳድራቸው ስለሆኑ የሚሰበሰበው ገቢ በገንዘብ ሚኒስቴር በኩል ማለፍ አለበት ይላሉ፡፡


ይጀመራል የተባለው የአየር ደህንነት ክፍያ የትኬት ክፍያን ሳይጨምር በሃገር ውስጥ በረራ ላይ 30 ብር እንዲሁም ወደ ውጭ በሚደረግ በረራ ላይ 1ዶላር ወይም 156 ብር እንደሆነ የሚናገሩት ዶ/ር ተኪ ማህዲ በአለም አቀፍ ደረጃ የሚሰራበት ነው፤የጎረቤት ሃገራት ከሚያስከፍሉት አንፃር በጣም ዝቅተኛ ነውም ይላሉ፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ የማቋቋሚያ አዋጅ እንዲህ አይነቱን ክፍያ እንዲሰበስብ ስለሚፈቅድለት አሰባሰቡ ከፋይናንስ ስርዓት ውጪ አይደለም የሚል ምላሽ ሰጥተዋል፡፡


ከአገልግሎት ክፍያ የሚሰበሰበው ገቢ ለኤርፖርት የሴኩዩሪቲ ቴክኖሎጂ ግዢ፣ ለአቭዬሽን ሴኩዩሪቲ የፀጥታ አካላት ሥልጠናና አቅም ግንባታ፣ ለአነፍናፊ ውሻ ግዥና ሥልጠና፣ ለጥገናና ማስፋፊያ እንዲሁም አጠቃላይ አሠራሩን ለማዘመን የሚውል መሆኑም በአዋጁ ተካትቷል።


የተለያዩ ትችቶች የተሰነዘሩበት የአቪየሽን ሴኩሪቲ አዋጅ ምክር ቤቱ ዛሬ ባካሄደው መደበኛ ስብሰባው በአብላጫ ድምጽ አጽድቆታል፡፡


ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ…..


ምንታምር ፀጋው


የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…


YouTube : https://shorturl.at/18TS1

WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx

X :- https://x.com/shegerfm?s=2

Recent Posts

See All
ፖሊስ በ"ፊንቴክ" ኢንቨስትመንት ማጭበርበር የተጠረጠሩ አርቲስቶች እና ቲክቶከሮች ላይ የጠየቀው ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ተፈቀደለት፡፡

ሚያዝያ 14/2018 ፖሊስ በ"ፊንቴክ" ኢንቨስትመንት ማጭበርበር የተጠረጠሩ አርቲስቶች እና ቲክቶከሮች ላይ የጠየቀው ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ተፈቀደለት፡፡ ፖሊስ ተጨማሪ 14 ቀን ለምርመራ እንዲፈቀድለት ባለፈው አርብ በነበረው ችሎት ጠይቆ ለውሳኔ ፍርድ ቤቱ ለዛሬ ቀጥሮ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በ"ፊንቴክ"(Finte

 
 
 

Comments


Sheger App Logo
iOS Store
Google Play

    ሸገር
102.1

ሸገር ኤፍ ኤም 102.1 አዲስ የሬዲዮ አቀራረብ መላና አዲስ ቃና ይዞ የቀረበ በሀገሪቱ የሚዲያ ገበያ ላይ መሪ ሚና የሚጫወት ጣቢያ ነው፡፡

ሁሌም ከሸገር ጋር ሁኑ
ሸገር የእናንተ ነው
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር! 

Sheger Radio | Sheger 102.1FM  © 2026 Adey Tensae Media & Entertainment PLC.  

bottom of page