የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን ማጠናከረን አላማው ያደረገ የፓን አፍሪካን ጉባኤ በመጪ ሳምንት በአዲስ አበባ ይካሄዳል ተባለ፡፡
- 12 hours ago
- 2 min read
ሐምሌ 16 2018
የህዝብ ለህዝብ ግንኙነትን ማጠናከረን አላማው ያደረገ የፓን አፍሪካን ጉባኤ በመጪ ሳምንት በአዲስ አበባ ይካሄዳል ተባለ፡፡
ይህ "ወርልድ ፐብሊክ ሰሚት አፍሪካ" በሚል የሚጠራ ጉባኤ በመጪው ሳምንት ከሐምሌ 22-23 2018 ዓ.ም በአፍሪካ የኢኮኖሚ ኮሚሽን መሰበሰቢያ ይካሄዳል ተብሏል፡፡
ጉባኤውን መቀመጫውን በሩሲያ ሞስኮ ያደረገው ወርልድ ፒፕልስ አሴምብሊ የተባለ አለም አቀፍ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅት፣ግሎባል ሰርቭ እና ግሎባል ብላክ ሴንተር ከተባሉ ድርጅቶች ጋር በትብብር ያዘጋጁታል ተብሏል፡፡
ከ700 በላይ ሰዎች ተሳታፊ ይሆኑበታል የተባለውን የፓን አፍሪካን ጉባኤ በተመለከተ ዛሬ በኢሊሌ ሆቴል ለጋዜጠኞች መግለጫ ተሰምቷል፡፡
ያኒና ዱቤይኮቭስካያ የጉባኤው አዘጋጅ ኮሚቴ ሀላፊ ናቸው፡፡
የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት የአንድን ሀገር ህዝብ ከሌላው የማስተሳሰር ትልቅ አቅም እንዳለው አብራርተዋል።
የአንድ ሀገር ህዝብ ከሌላው ጋር ያለምንም መቃረን እና ግጭት በስፖርት ፣ በባህል ፣ በት/ት ፣ በስነ ጥበብ እና በሌላውም አንድ ሆኖ መቆም እንደሚችል አብራርተዋል፡፡
የአፍሪካ ሀገራት እርስ በርስ እንዲሁም አፍሪካዊያን ከተቀረው አለም ጋር ያላቸውን የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ማጠናከር የጉባኤው ዓላማ ነው ተብሏል፡፡
ባለፈው አመት የጉባኤው አዘጋጅ ወርልድ ፒፕልስ አሴምብሊ ከ160 በላይ ሀገሮች የታደሙት የመጀመሪያ አለም አቀፍ ጉባኤን በሩሲያ ካደረገ በኋላ ቀጣይ አለም አቀፍ የህዝብ ለህዝብ ጉባኤን በህንድ እንዲሁም በላቲን አሜሪካዋ ብራዚል ማድረጉን የኮሚቴው አስተባባሪ ያኒና ተናግረዋል፡፡
የአፍሪካን ሀገራት ያሰባስባል የተባለው አህጉራዊ ጉባኤም በአፍሪካ ምድር ለመጀመሪያ ጊዜ በአዲስ አበባ በመጪው ሳምንት ይካሄዳል ተብሏል፡፡
በመጪው ሳምንት በሚካሄደው የፓን አፍሪካን ጉባኤ ላይ ከ20 በላይ የፓናል ውይይቶች የሚደረጉ ሲሆን በባህል ፣ በትምህርት ፣ በወጣቶች፣በቅርስ እና ሌሎችም ጉዳዮች ዙሪያ ያተኩራሉ ተብሏል፡፡
የጉባኤው አዘጋጅ ኮሚቴ መሪ የሆኑት ያኒና ዱቤይኮቭስካያ እንዳስረዱት በዚህ ጉባኤ ወቅት በአፍሪካ ተግባራዊ የሚደረጉ ሶስት ፕሮጀክቶችም ይፋ ይሆናሉ።
የዛምቤዚ ወንዝ የሚያስተሳስራቸው ሀገሮች በጋራ የሚሰሩበት የምርምር ስራ ፣ በአንድነት ዙሪያ የአፍሪካ አርቲስቶችን የሚያስተባብር እና በአፍሪካ ያሉ ምግባረ ሰናይ ድርጅቶችን የተመለከቱ ፕሮጀክቶች ይፋ ይደረጋሉ ተብሏል፡፡
በኪነ ጥበብ ኢግዚቢሽኑ ላይ የኢትዮጵያ የካሜሩን ፣ የጋና ፣ የኬኒያ እና በአጠቃላይ የ16 የአፍሪካ ሀገር አርቲስች ይሰባሰቡበታል ተብሏል፡፡
በዚህ ጉባኤ ላይ ከሚሳተፉ ተወካዮች የሚበዙት የሲቪል ማህበረሰብ ተወካዮችና ወጣቶች እንደሚሆኑም ተነግሯል፡፡
የአህጉራዊ ጉባኤው ሌላኛው ተባባሪ አዘጋጅ የሰርቭ ግሎባል ምክትል ካንትሪ ዳይሬክተር አቶ ታሪኩ ነጋሽ በዚህ ጉባኤ ላይ በህዝብ ለህዝብ የዲፕሎማሲ ስራ የላቁ ተብለው የሚመረጡ 10 አፍሪካዊያንም እውቅና ይሰጣቸዋል ብለዋል፡፡
የጉባኤው አዘጋጅ የሩሲያው ወርልድ ፒፕልስ አሴምብሊ ከዘጠኝ አመት በፊት የተመሰረተ ድርጅት ሲሆን በስሩ ከ150 በላይ ሀገሮች ከ3 ሺህ በላይ ድርጅቶች አባል የሆኑበት ነው ተብሏል፡፡
ቴዎድሮስ ወርቁ
_edited.jpg)

Comments