ከተሽከርካሪ መድን ሽፋን ባሻገር ያሉ የመድን ሽፋን አገልግሎቶች ለምን ትኩረት ተነፈጋቸው?
- 3 hours ago
- 1 min read
ሐምሌ 8/2018
በኢትዮጵያ የመድን አገልግሎት መሰጠት ከጀመረ አንድ ክፍለ ዘመን ተሻግሯል።
በተለይ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በዘርፉ የሚቀላቀለው ባለ መዋለነዋይ እየጨመረ መምጣት የመድን አገልግሎት ሰጪ ተቋማትን ቁጥር ወደ 19 እንዳደረሰውም መረጃዎች ያሳያሉ።
ሰዎች በተለይ የጤና፣ የህይወት፣ የቁስ እና የረዥም ጊዜ የአካል ጉዳት የመድን አገልግሎትን እንዲጠቀሙ የዘርፉ ባለሙያዎች ይመክራሉ።
ይሁን እንጂ በኢትዮጵያ በብዛት የተለመደው የሞተር ወይም የተሽከርካሪ ኢንሹራንስ ነው።
አገልግሎቱን የሚሰጡ ተቋማት የግብርና ኢንሹራንስን ጨምሮ ሌሎችንም የመድን ሽፋኖች ቢሰጡም ግን ሌሎች አገልግሎቶች ላይ ክፍተት እንዳለባቸው ይነገራል።

ለመሆኑ ለተሽከርካሪ መድን ሽፋን አገልግሎት የተሰጠውን ትኩረት ያህል ሌሎቹ የመድን ሽፋን አገልግሎቶች ለምን ትኩረት ተነፈጋቸው? ምክንያቱስ ምንድነው?
የኢትዮጵያ ጠለፋ መድን አክሲዮን ማህበር የስትራቴጂ እና ቢዝነስ ዴቨሎፕመንት ምክትል ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ ፍቅሩ ፀጋዬን ጠይቀናቸዋል።
የጤና ፣ የህይወትና የግብርና የመድን ሽፋን ትኩረት አነስተኛ የሆነበት ምክንያት ዘርፈ ብዙ ነው ይላሉ።
የህብረተሰቡ የግንዛቤ ክፍተት እና በቴክኖሎጂ የተደገፈ የመድን ሽፋን አለመቅረብ ከምክንያቶቹ ውስጥ መሆኑን ጠቅሰዋል።
እነዚህ የመድን ሽፋን አገልግሎቶች እንደ መሰረታዊ ፍላጎቶች ሊታዩ እና ከፍተኛ ትኩረትም ሊሰጣቸው ይገባል ብለዋል።
የመድን ሽፋን አገልግሎት እንዲስፋፋ በመንግስት በኩል ትኩረት ተሰጥቶት እየተሰራበት መሆኑን አቶ ፍቅሩ ነግረውናል።
ነገር ግን ከተሸከርካሪ የመድን ሽፋን ውጪ ያሉ አገልግሎቶችን ህብረተሰቡ እንዲጠቀማቸው ለማድረግ መንግስት አስገዳጅ መመሪያዎችን ማዘጋጀት እንዳለበትም ያነሳሉ። ይህም በዘርፉ ላለው ችግርም መፍትሄ ይሆናል ብለው ያምናሉ።
በኢትዮጵያ የመድን ሽፋን እየሰጡ ያሉ ተቋማት የአገልግሎት አሰጣጥ ስርዓታቸው ከቀድሞው በተሻለ መልኩ እያደገ መምጣቱንም አቶ ፍቅሩ ፀጋዬ ተናግረዋል።
ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ…
ፍቅሩ አምባቸው

