ከቀናት በፊት በተከበረው የፋሲካ በዓል ወቅት የሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት አንድ ኪሎ ስጋ በ650 ብር እንዲሸጡ ተወስኖ በዚሁ መሰረት ሲያቀርቡ ቆይተዋል።
- Apr 23
- 2 min read
ሚያዝያ 15/2018
ከቀናት በፊት በተከበረው የፋሲካ በዓል ወቅት የሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት አንድ ኪሎ ስጋ በ650 ብር እንዲሸጡ ተወስኖ በዚሁ መሰረት ሲያቀርቡ ቆይተዋል።
ዋጋው አያዋጣንም ያሉ አንዳንድ የሸማቾች ህብረት ስራ ማህበራት ግን በሱቆቻቸው ስጋ አልነበረም።
ለመሆኑ ማህበራቱ ያለ ትርፍ አንዳንዴም በኪሳራ ምርቶቹን እንዲሸጡ ማድረግ ትክክል ነው ወይ?
የህብረት ስራ ማህበራት የተቋሙበት አላማ ሸማቾች ጥራት ያለው ምርት በተመጣጣኝ ዋጋ እንዲያገኙ፤ አምራቾችም ለምርታቸው ተገቢው ክፍያ እንዲፈጸምላቸው ማድረግ የሚል ነው።
ብዙዎችም በተለይ የፍጆታ ምርቶችን በእነዚሁ ማህበራት ከተቋቋሙ ሱቁች በተመጣጣኝ ዋጋ ማግኘት እንደቻሉ ይናገራሉ።
በሌላ በኩል የሸማች ህብረት ስራ ማህበራት ምርቶችን የሚሸጡበት ዋጋ ገደብ የተቀመጠለት ስለሆነ ሊኪሳራ እየዳረጋቸው ነው የሚሉ ሰዎች አሉ።
ለአብነትም ከቀናት በፊት በተከበረው የፋሲካ በዓል ሠሞን ማህበራቱ አንድ ኪሎ ስጋ ከ650 ብር በላይ እንዳይሸጡ በመወሰኑ ሲቸገሩ እንደነበር ያነሳሉ።
በዚህ ዋጋ ሸጠን ኪሳራ ውስጥ አንገባም ያሉም እንዳሉ ሠምተናል።
ለመሆኑ የህብረት ስራ ማህበራት እየከሰሩ ጭምር ምርቶችን ለተጠቃሚዎች እንዲያቀርቡ የማድረግ አሰራር አለ ወይ? ስንል ፤ የኢትዮጵያ ኅብረት ሥራ ኮሚሽን ዋና ኮሚሽነር ጌትነት ታደሠን ጠይቀናል።
የህብረት ስራ ማህበራት ያስፈለጉት በአምራቹ እና ሸማቹ መካከል ያለውን የግብይት ሠንሠለት ለማሳጠር ነው የሚሉት አቶ ጌትነት በዚህ ሂደት ዋጋም መወሰን እንደሚችሉ ተናግረዋል።
ትርፋቸው በረጅም የግብይት ሠንሠለት ምርቶቹን እንደሚያገኘው ነጋዴ ይሁን ማለት ግን ትክክል አይደለም ሲሉ አክለዋል።
ከህብረት ስራ ማህበራት ጋር በተገናኘ የሚነሳው ሌላው ጉዳይ አቅማቸው ነው።
በተለይ የገንዘብ አቅማቸው የሚፈልጉትን ምርት ከሚፈልጉት ቦታ በሚፈልጉት መጠን ገዝተው ለተጠቃሚው እንዲያቀርቡ የሚያስችላቸው እንዳልሆነ ይነሳል።
ስለዚሁ የጠየቅናቸው አቶ ጌትነት የገንዘብ አቅማቸውን ማሳደግ በዋናነት የራሳቸው የማህበራቱ እንደሆነ ተናግረዋል።
እሱ እንዳለ ሆኖ ካፒታላቸውን እንዲያሳድጉ የሚረዷቸውን አማራጭ መንገዶችም የህግ ማሻሻያ በማድረግ ጭምር ለመፍጠር እየሰራን ነው ብለውናል።
ከአንድ ሺህ ብር በታች የሆነ የካፒታል አቅም ያላቸው የህብረት ስራ ማህበራት እንደተገኙ የነገሩን አቶ ጌትነት እነዚህ ከሌሎች ጋር ተዋህደው እንዲሰሩ ተደርጓል ብለዋል።
በስም ብቻ የሚታወቁ፤ አድራሻ የሌላቸው እና ለሪፖርት ፍጆታ ብቻ ሲጠቀሱ የነበሩ 31 ሺህ 292 ማህበራት ደግሞ እንዲከስሙ መደረጉን ነግረውናል።
ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ….
ንጋቱ ረጋሣ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
YouTube : https://shorturl.at/18TS1
Telegram : https://shorturl.at/68aeK
Facebook፡ https://shorturl.at/tm5Q4
WhatsApp : https://shorturl.at/8vwRx
X :- https://x.com/shegerfm?s=2
LinkedIn: https://shorturl.at/Vfe6i
Tiktok : https://shorturl.at/lhYiv
Instagram: https://shorturl.at/9X4S7




Comments