ነሀሴ 27 2017 - ሆራይዘን አዲስ ጎማን ከሀገር ውስጥ ባለፈ ለጎረቤት ሀገራት ለማቅረብ መታቀዱን ተነገረ፡
- sheger1021fm
- Sep 2
- 1 min read
ሆራይዘን አዲስ ጎማን ከሀገር ውስጥ ባለፈ ለጎረቤት ሀገራት ለማቅረብ መታቀዱን ተነገረ፡፡
ይህን የሰማነው የሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ያዘጋጀው አውደርዕይ በተከፈተበት ወቅት ነው፡፡
በአውደርዕዩ 45 በሚድሮክ ኢንቨስትመን ግሩፕ ስር የሆኑ ኩባንያዎች ምርቶቻቸውን አቅርበዋል፡፡
አንዳንድ ኩባንያዎች በእዳ እና በሌሎች ምክንያቶች በሆነ ወቅት ኪሳራ ውስጥ ገብተው ሰራተኞቻቸውን እስከ መበተን ድረስ የሚያሰጋ አደጋ ውስጥ ነበሩ ያሉት የሚድሮክ ኢንቨስትመን ግሩፕ ዋና ስራ አስፈዋፃሚ አቶ ጀማል አህመድ ናቸው፡፡

ሚድሮክ የ5 አመት እቅድ በማውጣት በሰራው ስራ ኩባንያዎች አሁን በጥሩ መንገድ እየሄዱ ነው ያሉት አቶ ጀማል አውደርዕዩም የተዘጋጀው ይህንን ስራ ለማሳየት ነው ብለዋል፡፡
የሆራይዘን አዲስ ጎማ የሽያጭ ኃላፊ አቶ ዘላለም ግርማ በዚህ ዘርፍ አብዛኛው ጥሬ እቃ ከውጪ እንደሚመጣ ይናገራሉ፡፡
አሁን ከአነስተኛ ተሽከርካሪዎች ጀምሮ እስከ ወታደራዊ መኪኖች ድረስ የሚጠቀሙት የመኪና ጎማ ሀገር ውስጥ እያመረቱ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
በጎማ ዘርፍ ለመሰማራት የጥሬ እቃ እጥረቱ አንዱ ፈታኝ ችግር ነው ያሉት አቶ ዘላለም 90 ከመቶ የሚሆነው ለጎማ ምርት የሚያገለግለው ጥሬ እቃ ከውጪ ይገባል፡፡
ከተመረተ በኋላም ህብረተሰቡ ለሀገር ውስጥ ምርት ያለው አመለካከት ሌላኛው ፈተና ነው ብለዋል፡፡
ሚድሮክ ኢንቨስትመንት ግሩፕ ከአመታዊ ትርፉ ውስጥ 10 ከመቶ የሚሆነው ለማህበራዊ ኃላፊነት እንደሚያውል ተጠቅሷል፡፡
79,000 ሰራተኞች በስሩ የያዘው ሚድሮክ በማዕድን ፣ ግብርና ፣ በሪል ስቴት እና በሌሎችም ዘርፎች የተሰማሩ ኩባንያዎች በስሩ ይገኛሉ፡፡
በረከት አካሉ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s








