ነሀሴ 16 2017 - በሀገር አቀፍ ደረጃ የሰላም ኮንፈረንስ ከሁለት ሳምንት በኋላ ይካሄዳል ተባለ፡፡
- sheger1021fm
- Aug 22
- 1 min read
በኢትዮጵያ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት አማካይነት የተዘጋጀ በሀገር አቀፍ ደረጃ የሰላም ኮንፈረንስ ከሁለት ሳምንት በኋላ ይካሄዳል ተባለ፡፡
ነሐሴ 29 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ በፌዴራል ደረጃ ኮንፈረንሱ ይካሄዳል ተብሏል፡፡
የቤት ስራ የሚሰጣቸው ተቋማት ይኖራሉ፤ በክትትልም የተሰጡ ስራዎች ከምን ደረሱ? በሚል ይገመገማሉ መሳተፍ የሚችሉ አካላት ሁሉ እንዲሳተፉም ጥሪ ይደረጋል ሲሉ የምክር ቤቱ ፕሬዝዳንት አቶ አህመድ ሁሴን ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

የሃይማኖት ተቋማትን ጨምሮ እድሮችን የመሳሰሉ የማህበረሰብ ተቋማት በሰላም ኮንፈረንሱ ላይ እንዲሳተፉ ከተደረገ የሚፈለገው ሰላም መምጣት ይችላልም ሲሉ ሀላፊው ተናግረዋል፡፡
ጦርነት ላይ ያሉ ወገኖች በቀጥታ የኮንፈረንሱ አካል ማድረግ ባይቻልም እነርሱም የኮንፈረንሱን ውጤት እንዲያውቁት ጫና ማድረግ አንዱ መንገድና ተልኳችን ነው ብለዋል፡፡
በየዓመቱ ጰግሜ ውስጥ የሚደረጉ የሰላም ጥሪዎች አሉ ነገር ግን ዘላቂ ለውጥ ሲመጣ አልታየም የተባሉት ኃላፊው ይሄኛው የተለየ ነው ለሁሉም የቤት ስራ የሚሰጥበት በመሆኑ ዝም ብሎ የሚዘጋጅ አመታዊ ኮንፈረንስ አይደለም ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
አዲስ እየተዘጋጀ ያለው የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶችን ረቂቅ በተመለከተ የተጠየቁት ሃላፊዎቹ ረቂቁ ቀድሞ ከተዘጋጀበት አሳሪ ይዘት እንዲላላ ሰርተናል፤ ይሁንና አሁንም ስላልጸደቀ እየተወያየን ነው የሚሻሻሉ ክፍሎች አሉ ሲሉ ሀላፊዎቹ ተናግረዋል፡፡
በኢትዮጵያ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት በኩል ይዘጋጃል የተባለው ሀገር አቀፍ ኮንፍረንስ ለሀገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ግብዓት ይሆናል ተብሏል።
የኔነህ ሲሳይ
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s












Comments