ታህሳስ 3/2018 ባለፉት 4 ወራት በህገ-ወጥ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ የሚገባ የኮንትሮባንድ እቃዎች ቁጥር መጨመሩን የገቢዎች ሚኒስቴር ተናገረ፡፡
- sheger1021fm
- 5 hours ago
- 1 min read
የገቢዎች ሚኒስቴር ይሄን ያለው ዛሬ በሕዝብ እንደራሴዎች ምክር ቤት ለፕላን በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የ4 ወር የስራ ክንው ሪፖርት ባቀረበበት ወቅት ነው፡፡
ሪፖርቱን ያቀረቡት የገቢዎች ሚኒስትር ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሴ ከገቢ ኮንትሮባንድ ከ8 ቢሊዮን ብር በላይ ፣ ከወጪ ኮንትሮባንድ ደግሞ 0.6 ቢሊየን ብር ማዳን መቻሉን ተናግረዋል፡፡
በድምሩ 8.7 ቢሊየን ብር የሚያወጣ የኮንሮባንድ እቃ መያዙን ተናግረዋል፡፡
የገቢ ኮንትሮባንድ በእጥፍ መጨመሩን የተናገሩት ሚኒስትሯ መድሃኒት፣ አልባሳት ጨርቃ ጨርቅ ፣ ኤሌክትሮኒክስ እና የማዕድን ውጤቶች ከፍተኛውን ድርሻ እንደሚይዝ አስረድተዋል፡፡
ባለፉት 4 ወራት 27 ኪሎ ግራም የሚመዝን ጥፍጥፍ ወርቅ መያዙንም ሚኒስትሯ አክለዋል፡፡
የወጪ ኮንትሮባንድ አብዛኛውን ድርሻ የሚይዘው የግብርና ምርት ነው የተባለ ሲሆን ባለፉት 4 ወራት ቅናሽ ማሳየቱ ተጠቁሟል፡፡
ሚኒስትር ዓይናለም በኮንትሮባንድ ሂደት ሲሳተፉ የተያዙ 353 ሰዎች በቁጥጥር ስር ውለው ጉዳያቸው እየተጣራ እንደሚገኝ ለቋሚ ኮሚቴው አስረድተዋል፡፡
በሌላ በኩል ባለፉት 4 ወራት ሚኒስቴር መ/ቤቱ 482.5 ቢሊየን ብር ገቢ መሰብሰቡ ተናግሯል፡፡
ይህም የእቅዱ 106 በመቶ ነው ተብሏል፡፡
ባለፉት 4 ወራት 444.3 ቢሊየን ብር ለመሰብሰብ ታቅዶ እንደነበር ያስታወሱት ሚኒስትሯ 482.5 ቢሊየን ብር ገቢ ሰብስበናል ብለዋል፡፡
ያሬድ እንዳሻው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
Website፡ https://www.shegerfm.com/
Telegram : https://t.me/ShegerFMRadio102_1
Facebook፡ https://web.facebook.com/Sheger102.1








