በአዲስ አበባ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ጉቦ እና የእጅ መንሻ፤ አካውንት ቁጥር እስከ መስጠት መድረሱ ተነገረ፡፡
- 6 minutes ago
- 1 min read
ሚያዝያ 30/2018
በአዲስ አበባ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ጉቦ እና የእጅ መንሻ፤ አካውንት ቁጥር እስከ መስጠት መድረሱ ተነገረ፡፡
በአዲስ አበባ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ለአገልግሎት የሚመጡ ሰዎችን ጉቦ የሚጠይቁ እንዳሉ የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባል ነው የተናገሩት፡፡
ጉቦ እና እጅ መንሻ መጠየቅ፤ አገልግሎት መስጠት ላይ እንቅፋት ሆኖ መቀጠሉም ከምክር ቤት አባል ተነስቷል፡፡
#ጉቦ ጠይቀው የተገኙት ላይም የሚወሰድባቸው እርምጃ እና የሚወሰኑ ውሳኔዎች ቀለል ያሉ ናቸው ተብሏል፡፡
ይህ መሆኑ ጉቦ ጠያቂዎቹ የበለጠ እየተደፋፈሩ እንደሆነና ቅጣቱ ሌሎችን ሊያስተምር እንዳልቻለ ተጠቅሷል፡፡

ይህ የተነገረው ዛሬ የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 3ኛ መደበኛ ጉባኤ ላይ ነው፡፡
ይህንን ተግባር ለማስቆም ምን እየተሰራ እንደሆነም ጥያቄ ቀርቧል፡፡
ከምክር ቤት አባል ለተነሳው ጥያቄ የሚመለከታቸው የስራ ሀላፊዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
በምላሻቸውም ችግሩ መኖሩን አምነው ይህንን ስር የሰደደውን #ሌብነት ለማስቆም የተለያዩ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ጥቆማዎች፣ ግምገማዎች እና የኦዲት ሪፖርቶችን በመንተራስ ችግሮቹን ለመፍተታ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡
በዚህም በ9 ወር ውስጥ 420 የሚሆኑ ባለሞያዎች እና አመራሮች በህግ ቁጥጥር ስር ውለዋል ተብሏል፡፡
ጉቦኝነት እና ሌብነት በከተማዋ እየተፈፀሙ ይገኛሉ ያሉት የስራ ሀላፊዎች፤ ባለሞያው እና አመራሩ ‘’ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል’’ በሚል ብሒል ያደገ ስለሆነ ችግሩን እንዳከፋው አንስተዋል፡፡
በሙስና እና በሌብነት ተሰማርተው በሚገኙት ላይ ሚወሰደው እርምጃና ተጠያቂነታቸው ቀድሞ ከነበረው ተሻሽሏል ብለዋል፡፡
ማንያዘዋል ጌታሁን

