top of page

በአዲስ አበባ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ጉቦ እና የእጅ መንሻ፤ አካውንት ቁጥር እስከ መስጠት መድረሱ ተነገረ፡፡

  • 6 minutes ago
  • 1 min read

ሚያዝያ 30/2018


በአዲስ አበባ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ጉቦ እና የእጅ መንሻ፤ አካውንት ቁጥር እስከ መስጠት መድረሱ ተነገረ፡፡


በአዲስ አበባ በመንግስት መስሪያ ቤቶች ለአገልግሎት የሚመጡ ሰዎችን ጉቦ የሚጠይቁ እንዳሉ የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባል ነው የተናገሩት፡፡


ጉቦ እና እጅ መንሻ መጠየቅ፤ አገልግሎት መስጠት ላይ እንቅፋት ሆኖ መቀጠሉም ከምክር ቤት አባል ተነስቷል፡፡


#ጉቦ ጠይቀው የተገኙት ላይም የሚወሰድባቸው እርምጃ እና የሚወሰኑ ውሳኔዎች ቀለል ያሉ ናቸው ተብሏል፡፡


ይህ መሆኑ ጉቦ ጠያቂዎቹ የበለጠ እየተደፋፈሩ እንደሆነና ቅጣቱ ሌሎችን ሊያስተምር እንዳልቻለ ተጠቅሷል፡፡



ይህ የተነገረው ዛሬ የአዲስ አበባ ከተማ ምክር ቤት 5ኛ ዓመት የስራ ዘመን 3ኛ መደበኛ ጉባኤ ላይ ነው፡፡


ይህንን ተግባር ለማስቆም ምን እየተሰራ እንደሆነም ጥያቄ ቀርቧል፡፡


ከምክር ቤት አባል ለተነሳው ጥያቄ የሚመለከታቸው የስራ ሀላፊዎች ምላሽ ሰጥተዋል፡፡


በምላሻቸውም ችግሩ መኖሩን አምነው ይህንን ስር የሰደደውን #ሌብነት ለማስቆም የተለያዩ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡


ጥቆማዎች፣ ግምገማዎች እና የኦዲት ሪፖርቶችን በመንተራስ ችግሮቹን ለመፍተታ እየተሰራ ነው ብለዋል፡፡


በዚህም በ9 ወር ውስጥ 420 የሚሆኑ ባለሞያዎች እና አመራሮች በህግ ቁጥጥር ስር ውለዋል ተብሏል፡፡


ጉቦኝነት እና ሌብነት በከተማዋ እየተፈፀሙ ይገኛሉ ያሉት የስራ ሀላፊዎች፤ ባለሞያው እና አመራሩ ‘’ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል’’ በሚል ብሒል ያደገ ስለሆነ ችግሩን እንዳከፋው አንስተዋል፡፡


በሙስና እና በሌብነት ተሰማርተው በሚገኙት ላይ ሚወሰደው እርምጃና ተጠያቂነታቸው ቀድሞ ከነበረው ተሻሽሏል ብለዋል፡፡


ማንያዘዋል ጌታሁን

Sheger App Logo
iOS Store
Google Play

    ሸገር
102.1

ሸገር ኤፍ ኤም 102.1 አዲስ የሬዲዮ አቀራረብ መላና አዲስ ቃና ይዞ የቀረበ በሀገሪቱ የሚዲያ ገበያ ላይ መሪ ሚና የሚጫወት ጣቢያ ነው፡፡

ሁሌም ከሸገር ጋር ሁኑ
ሸገር የእናንተ ነው
ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር! 

Sheger Radio | Sheger 102.1FM  © 2026 Adey Tensae Media & Entertainment PLC.  

bottom of page