በመጪው ዓመት የመንግስትን ገቢ ለማሳደግ ያግዝ ዘንድ ከታክስ ነፃ እና የግብር እፎይታ አሰራሮች ሊቀሩ መሆኑ ተሰምቷል፡፡
- 10 hours ago
- 1 min read
ሰኔ 5/2018
በመጪው ዓመት የመንግስትን ገቢ ለማሳደግ ያግዝ ዘንድ ከታክስ ነፃ እና የግብር እፎይታ አሰራሮች ሊቀሩ መሆኑ ተሰምቷል፡፡
በዚህም ከዚህ ቀደም ከጉምሩክ ቀረጥ ነፃ ተደርገው ወደ ሀገር ይገቡ የነበሩ እቃዎች ከመጪው በጀት ዓመት ጀምሮ ቅናሽ የጉምሩክ የቀረጥ ምጣኔ እንዲከፍሉ ይደረጋል ተብሏል፡፡
በዚህም 22.5 ቢሊዮን ብር ለመሰብሰብ መታቀዱን የገንዘብ ሚኒስቴር ለፓርላማው ያቀረበው ረቂቅ በጀት ያሳያል፡፡
በተጨማሪም የገቢ ግብር እፎይታ አሰራርን ቀሪ በማድረግ የግብር እፎታ ይሰጣቸው የነበሩ በቅናሽ ምጣኔ ግብር በማስከፈል ሌላ 22 ነጥብ 5 ቢሊየን ብር እንደሚሰበሰብ በረቂቁ ሰፍሯል፡፡
ከዚህ ቀደም የሴቶችን ስራ ለማቃለል በሚል የልብስና የእቃ ማጠቢያ ማሽኖች ከቀረጥ ነፃ እንዲገቡ ከተፈቀዱ መካከል ነበሩ፡፡
በተጨማሪም የጤናና የግብር ዘርፍ የተለያዩ መሳሪያዎች ከቀረጥ ነፃ ይገቡ እንደነበርም ይታወሳል፡፡
ለአካል ጉዳተኞች የሚያግዙ የተለያዩ እቃዎችም ከጉምሩክ ቀረጥ ነፃ ነበሩ፡፡
በሌላ በኩል መንግስት ገቢውን ለማሳደግ የኤክሳይዝ ታክስን ለማስተዳደር ዘመናዊ የቴምብር ሥርዓትን በመዘርጋት ከዚህ ቀደም ባልነበረ አዲስ አሰራር ኢኮኖሚው ተጨማሪ 33.8 ቢሊየን ብር እንዲያገኝ እቅድ ተይዟል ተብሏል፡፡

በዚህም የግብር እፎይታን እና ከጉምሩክ የቀረጥ ነጻ አሰራርን በማስቀረትና የኤክሳይዝ ታክስን ለማስተዳደር አዲስ ስራ ላይ በማዋል ዘመናዊ የቴምብር አሰራርን አሰራር በድምሩ 78.9 ቢሊዮን ብር በመሰብሰብ የመንግስትን ገቢ ከፍ ለማድረግ ታቅዷል፡፡
ይህም ከዚህ ቀደም ኢኮኖሚው ከሚያውቃቸው የገቢ ምንጮች የሚገኝ አዲስ የገቢ ምንጭ ይሆናል እንደማለት ነው፡፡
በቀጣዮቹ አመታት የመንግስትን ከግብር የሚገኝ ገቢ ለማሳደግ የፖሊሲ ማሻሻያዎች ፣ የመንግስት የውጪ ፖሊሲ ማሻሻያዎች እንዲሁም የበጀት ጉድለት አሸፋፈንና የብድር ፖሊሲ ማሻሻያዎች እየተደረጉ መሆኑንም ሰነዱ ተጠቅሷል፡፡
በ2019 በጀት ዓመት በአጠቃላይ ከቀጥተኛ ግብር ወደ 1.5 ትሪሊዮን ብር ለመሰብሰብ እቅድ መያዙን ከረቂቅ በጀቱ ተመልክተናል፡፡
ታክስ ካልሆኑ ምንጮች የሚገኙ የመንግስት ገቢዎችንም አሟጦ ለመጠቀም የሚያስችሉ ስራዎች ይሰራሉ ብሏል የገንዘብ ሚኒስቴር፡፡
በተለይም ከቅጣትና ከመንግስት የአገልግሎት ሽያጭ እንዲሁም ከመንግስት ኢንቨስትመንት የሚገኝን ገቢ በወቅቱ በመሰብሰብ በአጠቃላይ ከታክስ እና ታክስ ካልሆኑ ምንጮች 1.6 ትሪሊዮን ብር የሀገር ውስጥ ገቢ በመጭው በጀት አመት ይሰበሰባል ይላል ረቂቅ በጀቱ፡፡
ትዕግስት ዘሪሁን





Comments