ሰኔ 25 2017 - ''የህዝብ እና የቤት ቆጠራ አልተካሄደም ማለት የበጀት ድልድሉ በግምት ነው የሚሰራው ማለት ነው'' የምክር ቤት አባል
- sheger1021fm
- 1 day ago
- 1 min read
‘’የህዝብ ቆጠራ ባልተደረገበት ሁኔታ የፌደራል መንግስት ለክልሎች የሚመድበው የድጎማ በጀት ምንን መሰረት ያደረገ ነው?’’ የሚል ጥያቄ ከምክር ቤት አባል ቀረበ፡፡
ለገንዘብ ሚኒስቴር ይህ ጥያቄ የቀረበው በትናንትናው እለት የ2018 ዓ.ም የፌደራል መንግስት በጀት ረቂቅ ላይ በምክር ቤት ውይይት በተካሄደበት ወቅት ነው፡፡
አቶ ባርጠማ ፍቃዱ የተባሉ የምክር ቤት አባል የህዝብ እና ቤት ቆጠራ ከተካሄደ ዓመታት መቆጠሩን አስታውሰው የህዝብ እና የቤት ቆጠራ አልተካሄደም ማለት የበጀት ድልድሉ በግምት ነው የሚሰራው ማለት ነው ብለዋል፡፡
ያለ ህዝብ ቆጠራ የሚካሄድ የበጀት ድልድል ፍትሃዊነት አይኖረውም ያሉት የምክር ቤት አባሉ የደመወዝ ማነስ፣ የልማት ጥያቄዎች እና የመሰረተ ልማት ጥያቄዎችም ከፍትሃዊነት ማነስ ነው የሚመጡት ሲሉ አስረድተዋል፡፡

የሀገሪቱ ህዝብ ቁጥር ከተቆጠር በርካታ ዓመታት እንደሆነው ያስረዱት አቶ ባርጠማ ግምት ካልሆነ በቀር የኢትዮጵያ ህዝብ ቁጥር ይሄ ነው የሚል የለም አንዱ 115 ሚልዮን ነው ይላል ሌላውም ደግሞ ሌላ ነው የሚለው ብለዋል፡፡
ማዕከላዊ ስታትስቲክስ አገልግሎት መረጃውን ከየት አምጥቶ የቤት እና የህዝቡን ብዛት እንደሚጠቅስም ግልጽ አይደለም ያሉት የምክር ቤት አባሉ ህዝብ ቆጠራ ሳይካሄድ የሚደረገው የበጀት ድልድል ፍትሃዊ ነው ወይ? ሲሉ ጠይቀዋል::
ለጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ አህመድ ሺዴ ናቸው፡፡ አቶ አህመድ ሺዴ በ2018 በጀት ላይ የህዝብ ቆጠራን ታሳቢ ተደርጎ እንዳልተዘጋጀ ተናግረዋል፡፡
መጠባበቅያ በጀት የሚያዘው ለእንደዚህ አይነት ጉዳዮች ነው ያሉት ሚኒስትሩ በሚቀጥለው ዓመት የሚደርስ አይመስለኝም ብለዋል፡፡
ቀጣይ ዓመት የምርጫ ሃላፊነት ያለበት ስለሆነ ብዙ ዳሰሳዎች እና ዝግጅቶች መሰራት አለባቸው ሲሉ የተናገሩት ሚኒስትሩ ምናልባት በ2019 ይመስለኛል የህዝብ እና ቤት ቆጠራው የሚካሄደው የዚያን ጊዜ በበጀቱ የሚካተት ነው የሚሆነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡
ያሬድ እንዳሻው
የሸገርን ወሬዎች፣ መረጃ እና ፕሮግራሞች ይከታተሉ…
📌 Telegram; https://t.me/ShegerFMRadio102_1
📌 YouTube: https://shorturl.at/P4mpX
📌 WhatsApp: https://tinyurl.com/ycxjmm3s
📌 Tiktok: https://bit.ly/44Dd6Il
Comments