ሰኔ 11 2017 - ኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይልን ለደቡብ ሱዳን፣ ሶማሊያና ታንዛንያ ለመሸጥ በዝግጅት ላይ መሆኗም ተነግሯል
- sheger1021fm
- 14 hours ago
- 1 min read
የናይል ተፋሰስ ሀገራት በጥናትና መረጃ ላይ የተመሰረተ ልምድ የሚለዋወጡበት ቀጠናዊ ትብብር መፍጠርን ታሳቢ ያደረገው አራተኛው አፍሪራን ዞናዊ ጉባኤ ዛሬ መካሄድ ጀምሯል፡፡
ቀጠናዊ ጉባኤውን የውጭ ጉዳይ ኢንስቲትዩት ባለቤት ሆኖ ያሰናዳው ሲሆን ቀጠናውን በኤሌክትሪክ ኃይል መሰረተ ልማት ማስተሳሰር የጋራ ለሆነ ልማት ያለው ፋይዳ ላይ መምከር የዘንድሮ አራተኛ ጉባኤ ሀሳብ ሆኖ ተመርጧል።
በዝግጅቱ ላይ ተገኙት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትሩ ጌዲዮን ጢሞቲዎስ(ዶ/ር) ከሰሃራ በስተደቡብ ባሉ ሀገራት ያለውን የኤሌክትሪክ አገልግሎት አነስተኛ ሽፋን አንስተው በተለይ በአፍሪካ በከተማና ገጠር ያለው ሽፋን በጣም የተራራቅና ብዙ መስራትን የሚፈልግ መሆኑን ጠቅሰዋል።

የኤሌክትሪክ መሰረተ ልማት ግንባታ ማሳደግን በተመለከተ ሲያነሱም ከፍጻሜው የደረሰው የህዳሴው ግድብን ጉዳይ አንስተዋል።
የህዳሴው ግድብ የኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን የቀጠናው ሀገሮችም ሀብት ሆኖ መቆጠር ያለበት እንደሆነ አብራርተዋል፡፡
የቀጠናው ሀገሮች በኤሌክትሪክ ኃይል ለማገናኘት በተሠራ ስራ ኢትዮጵያ ለሱዳን ኬንያና ጅቡቲ የኤሌክትሪክ ኃይል በሽያጭ እንደምታቀርብ አንስተው ይሄንን በኤሌክትሪክ ቀጠናውን የማስተሳሰር ሰራን በማስፋት ለደቡብ ሱዳን ሶማሊያና ታንዛንያም ኤሌክትሪክ ሃይል ለመሸጥ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑን ሚኒስትሩ ጠቅሰዋል፡፡
የውሃና ኢነርጂ ሚኒስትሩ ኢንጂነር ሃብታሙ ይተፋ በዓለም ዙሪያ ከ700 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ኤሌክትሪክ የማያገኝ መሆኑን በማንሳት ከዚህ ውስጥ ወደ 600 ሚሊየን የሚሆነው ህዝብ ከሰሃራ በስተደቡብ ያለ መሆኑን አንስተዋል፡፡
ቴዎድሮስ ወርቁ
Comments