ሠራተኞቻቸውን የጡረታ መዋጮ በጊዜው ገቢ የማያደርጉ የግል ድርጅቶች ራሳቸውን ላልተገባ ቅጣት እና ወለድ እየዳረጉ ነው ተባለ።
- sheger1021fm
- 33 minutes ago
- 1 min read
ጥር 5/2018
ሠራተኞቻቸውን የጡረታ መዋጮ በጊዜው ገቢ የማያደርጉ የግል ድርጅቶች ራሳቸውን ላልተገባ ቅጣት እና ወለድ እየዳረጉ ነው ተባለ።
ሃብት ንብረታቸውን ሸጦ የጡረታ መዋጮው ገቢ እንዲሆን እስከ ማድረግ የሚደርስ እርምጃ ሊወስድባቸው እንደሚችልም የግል ድርጅት ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር አሳስቧል።
አንድ እና ከአንድ በላይ ሠው የቀጠረ ማንኛውም የግል ድርጅት ሠራተኛውን ወደ ጡረታ አቅድ የማስገባት ግዴታ እንዳለበት የግል ድርጅት ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር አሳስቧል፡፡
ሠራተኛው ወደ ጡረታ ስርአቱ መግባት ያለበት ከተቀጠረ ከአርባ አምስት ቀናት በኋላ እንደሆነ የድርጅቱ ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ አባተ ምትኩ ተናግረዋል።
አብዛኞቹ ቀጣሪ ድርጅቶች ግን ሠራተኛው ኮንትራት ነው ወይም ጊዜያዊ ነው በሚል ይህን ግዴታ ያለ ማክበር ዝንባሌ ይታይባቸዋል ብለዋል።

የጡረታ መዋጮ ከሠራተኛውም ፤ ከቀጣሪውም ድርጅት ቀንሶ በጊዜው ገቢ ማድረግ ላይ በብዙዎቹ የግል ድርጅቶች ላይ አሁንም ሰፋ ያለ ችግር ይታያል ተብሏል።
ቀጣሪ ድርጅቶች በዚህ ምክንያት ላልተገባ ቅጣት እና ወለድ እየተዳረጉ እንደሚገኙ አቶ አባተ ተናግረዋል።
የጡረታ መዋጮውን በጊዜው ገቢ የማያደርጉ ድርጅቶች ሃብት ንብረታቸው እንዲሸጥ የሚያደርግ ጭምር ሊደረግ ይችላል ብለዋል።
አሁን ላይ በግል ድርጅቶች የሚሰሩ 2 ነጥብ 5 ሚሊየን ሰዎች በጡረታ አቅድ መሸፈናቸው ተጠቅሷል።
በግል ድርጅቶች ሲሰሩ ቆይተው ጡረታ ለወጡ ከ240 ሺህ በላይ ሰዎች ክፍያ እየተፈጸመ እንደሚገኝም ስራ አስፈጻሚው ተናግረዋል።
ከጡረታ መዋጮ የተሰበሰበ ከ135 ቢሊየን ብር በላይ አለም ብለዋል።
በስራ ላይ ያሉ ሰራተኞች በየጊዜው የደመወዝ ማሻሻያ ሲደረግላቸው ይታያል ፤ ጡረተኞች ግን የሚያገኙት ክፍያ በጣም አነስተኛ ነው በሚል
ስለሚቀርቡ ቅሬታዎች የተጠየቁት ስራ አስፈጻሚው ተከታዩን ምላሽ ሰጥተዋል።
የግል ድርጅት ሠራተኞች ማህበራዊ ዋስትና አስተዳደር በዚህ አመትም 56 ቢሊየን ብር የጡረታ መዋጮ ለመሰብሰብ አቅጃለሁ ብሏል።
ንጋቱ ረጋሣ








